Tuesday, May 14, 2013

ታላቅ ህዝባዊ ጥሪ በሰማያዊ ፓርቲ



ማያዊ ፓርቲ ሚያዚያ 29 2005 ዓም የአፍሪካ ህብረት የወርቅኢዮቤልዮ በአል በሚከበርበት ሰአት ሰላማዊ ሰልፍ መጥራቱ ይታወቃል:: ድርጅቱ ይህንን ህዝባዊ ጥሪ ያቀረበበት ዋናው ምክንያት ከዚህ ቀደም ለመንግስት የተለያዩ ጥያቄዎቹን በተደጋጋሚ ያቀረበ ቢሆንም፤ እስካሁን ድረስ መልስ ባለማግኘቱ አጋጣሚውን በመጠቀም ድምጹን ለዓለም ዓቀፉ ማህበረሰብ ለማሰማት መሆኑን በመግለጫው አስፍሯል:: በተጨማሪም ዜጎች ህገመንግስቱ ያጎናፀፋቸው ሰላማዊ ሰልፍ የማድረግ መብት ቢኖራቸውም፤ መንግስት በተደጋጋሚ የጅምላ ግድያ በመፈጸም ሃሳብን መግለጽ እና ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግ እንዳይታሰብ ማድረጉ በመግለጫው አስቀምጧል:: 

ድርጅቱ ባቀረበው ጥያቄ ከጠቀሳቸው ነጥቦች መካከል ለፍትህና ዲሞክራሲያዊ ስርዓት መስፈን የሚታገሉ ነገር ግን በአሸባሪነት ስም የታሰሩ ጋዜጠኞች፣ የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲ መሪዎችና፣ አባላት እንዲፈቱ ፤ የዜጎች ሰብዓዊና ሕገ መንግስታዊ መብቶችን በመጣስ ለዘመናት ከኖሩበት ቦታ በታጠቁ ኃይሎች በማፈናቀል የዘር ማጥፋት ወንጀል የፈፅሙ አካላት ለፍርድ እንዲቀርቡና የተፈናቀሉት ዜጎችም በአስቸኳይ ወደየመኖሪያቸው ተመልሰው እንዲቋቋሙ በመንግስት ድጋፍ እንዲደረግላቸው ፤ መንግስት በኃይማኖታችን ጣልቃ አይግባ፣ የእምነት ስርዓታችንንና የሃይማኖት መሪዎቻችንን ምርጫ እምነታችን በሚፈቅደው መንገድ ብቻ እናከናውን ያሉ የእስልምና ሃይማኖት ተከታይ ዜጎችን በአሸባሪነት በመወንጀልና በመክሰስ ማሰሩንና በግፍ ማንገላታቱን እንዲያቆምና ያነሷቸውንም ጥያቄዎች በሠላማዊ መንገድ ፍትህ እንዲሰጣቸው ፤ እንዲሁም መንግስት የኑሮ ዉድነትን ፣ የሥራዓጥነትንና፣ በሙስና የተዘፈቁ የመንግስት ሌቦችን የሚቆጣጠርባቸውን ትክክለኛ መንገዶችና ፖሊሲዎች በማዉጣት ሐገራችንን ከቀውስና ዜጎችንም ከሰቆቃ እንዲያወጣ የሚሉት ይገኙበታል:: 

የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሔራዊ ንቅናቄ የኢትዮጵያ ህዝብ በኢኮኖሚ በልፅጎና ሙሉ ነፃነቱ ተጠብቆለት የሚኖርባት ሃገር ኢትዮጵያን ለመመስረት ፣ በኢትዮጵያ ማንኛውም የህዝብ መብቶች በእኩልነት እንዲከበሩና ፣ ለሁሉም እኩል የሆነ ዲሞክራሲያዊ ስርዓትን በሃገራችን ኢትዮጵያ ለመገንባት በፅናት የሚታገል ፣ በወጣቶች የተመሰረተና የሚመራ ፣ ህዝባዊ ንቅናቄ ነው:: 

ሰማያዊ ፓርቲ በመግለጫው የጠቀሳቸው አራት ጥያቄዎች የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሔራዊ ንቅናቄ መልስ እንዲያገኙ ከሚታገልላቸው ዋና ዋና የህዝብ ጥያቄዎች መካከል ውስጥ የሚገኙና ዘረኛው የወያኔ/ኢህአዴግ መንግስት በዘረጋው የጭቆናና የግፍ መረብ በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ በግዴለሽነት በግልፅ በአደባባይ ከሚፈፅመው ስቃይ ፣ መከራና ፣ እንግልት ጥቂቶቹ በመሆናቸው ፤ የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሔራዊ ንቅናቄ ሰማያዊ ፓርቲ ያቀረበው ወቅታዊና ተገቢ የሰላማዊ ሰልፍ ጥሪን ሙሉ ለሙሉ የተቀበለው መሆኑን በአፅንዎት ይገልፃል:: 

ስለሆነም የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሔራዊ ንቅናቄ ሰማያዊ ፓርቲ ላቀረበው ህዝባዊ ጥሪ አስፈላጊውን ትብብርና ድጋፍ ለማድረግ ቃል በመግባት ለተግባራዊነቱም በትጋት ከልብ የሚሰራ መሆኑን በጥብቅ ያረጋግጣል:: 

የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሔራዊ ንቅናቄ የሰማያዊ ፓርቲ ጥሪ ህዝባዊ በመሆኑ ፤ በዚህ ዘረኛ የወያኔ/ኢህአዴግ መንግስት ከልክ ያለፈ ጭቆና ፣ ረገጣና ፣ እንግልት ደርሶብኛል የምትሉ ንፁሃን ኢትዮጵያውያን ዜጎችና ፣ በምንወዳት ሃገራችን ለህዝብ የሚበጅ ቀና ለውጥን የምትመኙ ሃገር ወዳድ ኢትዮጵያዊያን በሙሉ ፤ እንዲሁም ተቃዋሚ የፖለቲካ ድርጅቶች ፣ የሃይማኖት ተቋማትና ፣ የሲቪክ ማህበራት ታላቅ ሃገራዊ ሃላፊነትና የህዝብ አደራ በጫንቃችሁ እንደተሸከማችሁ በመገንዘብ ፤ የሚጠበቅባችሁን ህዝባዊ ተልኮ መፈፀም ታሪካዊ ግዴታችሁ መሆኑን በመረዳት ፤ ከሰማያዊ ፓርቲ ህዝባዊ የሰላማዊ ሰልፍ ጥሪ ጎን እንድትቆሙ ሲል በጥብቅ እያሳሰበ ፤ ሃገራዊ ጥሪውን በአክብሮት ያቀርባል:: የሰማያዊ ፓርቲ ጥሪ የሁሉም ሃገር ወዳድ ኢትዮጵያዊ ጥሪ ነው! 

ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!

የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሔራዊ ንቅናቄ

No comments:

Post a Comment