Monday, January 28, 2013

የአርቲስቷ ባል ኢትዮጵያ ውስጥ ታሰረ


ጥር ፳ (ሀያ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-ተቀማጭነቱ ለንደን የሆነው የኢትዮጵያ ዳንኪራ የዳንስ ግሩፕ አባል የሆነችው አርቲስት እስከዳር ታምሩ እና ባለቤቷ አበበ ወንድምአገኝ በደህንነት ሃይሎች የዛሬ ሳምንት ቦሌ አካባቢ ታሰሩ።

እንደ ደብረ ብርሀን ብሎግ ዘገባ ፤ጥንዶቹ የሁለት አመት ልጃቸውን ይዘው ከሎንዶን ወደ አዲስ አበባ የሔዱት በአል ለማክበር ነበር።እዚያ እንደደረሱ ከታሰሩ በሁዋላ አርቲስት እስከዳር ስትለቀቅ ባለቤቷ አበበ አሁንም እስር ቤት ይገኛል።

አቶ አበበ ፍርድ ቤት ቀርቦም የሃያ ቀን ቀጠሮ የተጠየቀበት ሲሆን፤ቤተሰቦቹ አዲስ አበባ ለሚገኘው ለእንግሊዝ ኤምባሲ ስለጉዳዩ አሳውቀዋል።

<<ምክንያቱ ፖለቲካዊ ነው የሚል>> ጥርጣሬ ቢኖርም፤እስካሁን የታሰረበት ምክንያት ምን እንደሆነ በግልጽ የታወቀ ነገር የለም።

ካሁን በፊት በተመሣሳይ ኮሜዲያን መስከረም በቀለ ከብዙ ኣመታት ቆይታ በሁዋላ የ አገሩንና የቤተሰቦቹን ናፍቆት ለመወጣት ወደዚያው ባቀናበት ጊዜ ገና ቦሌ አውሮፕላን ማረፊያ እንደደረሰ በሴኩሪቲዎች ተይዞ መታሰሩ ይታወሳል።

ጭንቀትና ስጋት ውስጥ የገባው መንግስት ወደ ቤተሰብ ለመጠየቅም ሆነ ለተለያየ ጉዳይ ወደ አገራቸው የሚሄዱ ኢትዮጵያውያን እዛ እንደደረሱ ለቀበሌ ሪፖርት ማድረግ አለባቸው የሚል ህግ ድረስ ማውጣት መድረሱን ያስታወሱ አስተያዬት ሰጭዎች፤ የአርቲስቷ ባል መታሰር የሚያመለክተውም የመንግስት ጭንቀት፣ጥርጣሬና ስጋት እየጨመረ መምጣቱን ነው ብለዋል።

No comments:

Post a Comment