Thursday, December 27, 2012

መንግስት የለም ወይ? መንግስት የለም ወይ? (ህዝብ)


ዘረኛው ህወሃት የኢትዮጵያ መንግስት እኔ  ነኝ ይላል። ህዝቡ ግን መንግስት የለም ወይ እያለ መጠየቁን አላቆመም። ህወሃት የመንግስት ቅርፅና መልክ የሌለው ቡድን ስለሆነ ኢትዮጵያ ውስጥ መንግስት አለ ለማለት አይቻልም። ህወሃት መንግስት መሆን ማለት ምን ማለት እንደሆነ ለማወቅ ብርቱ የሆነ የአቅም ችግር አለበት። ይሄን ደካማነቱን የተመለከተ ህዝብ ነው ድምጹን ከፍ አድርጎ መንግስት የለም ወይ ? መንግስት የለም ወይ? ብሎ የጠየቀው።ህወሃት የመንግስትነት ባህሪይ ቢኖረው ኑሮ ይሄን ድምጽ ማድመጥ በቻለ ነበር። እንዲህ ያለውን ድምጽ አሁን በዚህ ዘመን ያለ ይቅርና በዚያ በጨለማ ዘመን እግዚአብሄር ሾመን የሚሉ ነገስታት እንኳ ቢሆኑ ያደምጡት ነበር።ህወሃት ከጨለማው ዘመን ነግስታት እንኳ የማይሻል እጅግ ኋላ ቀር መሆኑን ከሚያሳዩን ድርጊቶቹ መካከል አንዱ ይሄው የህዝቡን ድምጽ መስማት አለመቻሉ ነው።

አንዳንድ ሰዎች ህወሃት የህዝቡን ድምፅ ለመስማት ፍላጎት እንዳይኖረው ያደረገው ምንድ ነው ብለው ይጠይቃሉ። መልሱ ተፈጥሮው ነው የሚል ነው። የህወሃት ተፈጥሮው የሚገለፀው በትእቢት እና በወንጀል ነው። ትዕቢቱና ሲፈፀመው የኖረው ወንጀሉ ደግሞ ከህዝብ ጋር አብሮ እንዳይኖር አድርገውታል። ህወሃት ራሱን “እኔ አውራ ነኝ ፤እኔ ከሌለው አገሪቷ ትፈርሳለች”እያለ በአደባባይ ሲፎክር መኖሩን እናውቃለን። ”እኔ ከሌለው አገር ትፈርሳለች” የሚለው አባባል አንደኛ የትዕቢቱ ማሳያ ሁለተኛ ደግሞ ለአገሪቷም ሆነ ለህዝቧ ምንም ኃላፊነት እንደማይሰማው የሚያስረግጥ አባባል ነው። በአጠቃላይ ህወሃት ራሱን አለማወቁና ወሰን ያጣው ትዕቢቱ የህዝብን ድምፅ እንዳይሰማ አግደውታል። ከዚህ ትዕቢቱ መላቀቅ ባለመቻሉም የህዝብድ ድምጽ አድምጦ ከህዝብ ጋር የመኖርን ጥበብ ሊያገኛት አልቻለም።

“እኛ አውራዎች ነኝ፤እኛ ከሌለን አገሪቷ ትፈርሳለች” የምትለዋ አባባል ያላዋቂዎች እንቶ ፈንቶ ብትሆንም እንዲህ እንላችኋለን፤

ህወሃቶች እውነት እውነት እንላችኋለን እናንተ ትሄዳላችሁ አገራችንም በሠላም ትኖራለች።የእናንተ አለመኖር አገራችንን አያፈርሳትም። እንዲያውም በተቃራኒው የእናንተ መኖር አገራችንን ከጎሬቤቶቿ ጋናንና ከኬኒያን ከመሳሰሉ አገራት በሁሉም ዘርፍ አንሳ እንድትታይ አደረጋት እንጂ የተሻለች አላደረጋትም።በእናንተ መኖር ምክንያት ዜጎች በተገኘው መንገድ ሁሉ መሰደድን መረጡ እንጂ ተረጋግተው በአገራቸው መኖርን አልመረጡም። ህወሃቶች አሁንም ስሙን እናንተ ባትኖሩ ኑሮ አገራችን ሠላሟ በዝቶ፤ ህዝቡ ተፋቅሮና ተከባብሮ፤ ብሄራዊ ስሜቱ በሚገባው ደረጃ ላይ ሁኖ፤ ሁሉም ኢትዮጵያ በአገሩ እኩል ከህግ በታች ሁኖ የሚኖርባት አገር በሆነች ነበር። ህወሃቶች አሁንም ስሙ የእናንተ መኖር አገሪቷን አፈርሳት እንጂ አልገነባትም።በእናንተ መኖር ምክንያት ህዝቡ “በአገራችን ሠላም አጣን”” ብሎ እንዲማረር ሆነ እንጂ ደስ ብሎት እንዲኖር አልሆነም።

ህወሃቶች የዚያች አገር መንግስት ለመሆን የሞራልም ሆነ የእውቀት ብቃት እንደሌላቸው ባለፉት ሁለት አስርተ ዓመታት በአገራችን ላይ የፈፀሟቸው በደሎች ህያዋን ምስክሮች ናቸው። አዲስ አበባ ውስጥ መንግስት የለም ወይ ? መንግስት የለም ወይ ? የሚለው ጥያቄ የመጠየቁ መነሻም ትግሬን ነፃ አወጣለሁ ብሎ የተነሳው ይሄ ዘረኛ ቡድን ያችን አገር ለመምራት የሚያስችል ስነ-ባህሪይ ማሳየት ባለመቻሉ ነው።ይህ ቡድን ራሱን ከጋረደበት ጥላቻ አላቆ እንደ ሰው ልጅ አስቦ ከሰው ልጆች ጋር አብሮ ለመኖር የሚያስችለውን ባህሪይ በሙሉ መልሶ ላያገኘው አጥቶታል። ይሄ ቡድን የሠላምን ዋጋ አያውቃትም።ይሄ ቡድን ነፃነት ማለት ምን ማለት እንደሆነም ገና አልገባውም።ህወሃት ከሌሎች ጋር አብሮ መኖርንም አያውቅም። ከጎጠኛ አስተሳሰቡ ለመላቀቅም የአዕምሮ ብስለት የለውም። ይህ የጎጠኞች እና የትዕቢተኞች ስብሰብ የሆነው ማፊያ ቡድን ሳይፈለግ ከተቆናጠጠበት የስልጣን ኮርቻ ላይ መውረድ አለበት። ኢትዮጵያን እንዲህ ያሉ ዘረኞችና ወንበዴዎች ሊመሯት አይገባም።

ህወሃት የሚመራት ኢትዮጵያ ህዝቧ ቀንና ማታ የሚያለቅስባት፤ልቅሶውን የሚያደምጥ መንግስት የሌለባት አገር ነች። ዛሬ በአዲስ አበባ ከተማ በሃና ማሪያም መንደር ነዋሪ የሆኑ ዜጎች ጥረውና ግረው የሠሩት ቤት ፈርሶ ህፃናት፤ እመጫቶች፤ በእድሜ የገፉ አዛውንት አባቶችና እናቶች ወደ ምትሄዱበት ሂዱ ተብለዋል።የት እንሄዳለን ብለው፤ የአገሪቷን ባንዲራ ይዘው የምንሄድበትን ቦታ ንገሩን ብለው ቢማፀኑም የያዙትን ባንዲራ ተነጥቀውከዚህሂዱየኢትዮጵያህዝብድሮምየሚኖረውመንገድላይነው ተብለው በህወሃት ቅጥረኛ ነፍሰ ገዳዮች አማካኝነት እንዲባረሩ ተደርጓል።

እናንተ ህወሃቶችና  ከጎናቸው የቆማችሁ ሌሎች ሆይ ነውር ነገር ታውቁ እንደሆነ ያደረጋችሁት እና የተናገራችሁት ነውር ነው።እናንተ ግን ነውር ነገርን ታውቃላችሁ ለማለት በጣም እንቸገራለን። ለማንኛውም እንዲህ እንላችኋለን፤

የኢትዮጵያ ህዝብ ጎዳና ላይ መኖር የጀመረው ህወሃት አገሪቷን መቆጣጠር ከጀመረ ወዲህ ነው።ዛሬ በሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎች በአዲስ አበባ ጎዳናዎች ላይ እንዲኖሩ የሆነው ህወሃቶች የአገሪቷን ሃብት ዘርፈው ለራሳቸው ብቻ በማድረጋቸው ነው።ዛሬ በውጭ አገራት ባንኮች ከኢትዮጵያ ህገ ወጥ በሆነ መንገድ ወጥቶ የተቀመጠው ብዙ ቢሊዮን ዶላር ዜጎች ጎዳና ላይ እንዲኖሩ ተደርጎ መሆኑን አበክረን ልናስታውሳችሁ እንወዳለን።ይሄ ዝሪፊያችሁ ነው የኢትዮጵያ ህዝብን ጎዳና ተዳዳሪ እንዲሆን ያደረገው እንጂ ሌላ አይደለም።

እናንተ ጎጠኛ ህወሃቶች ስሙ!!!

ዛሬ እናንተ ልጆቻችሁን በአሜሪካና በአውሮፓ እንዲሁም በቻይና ልካችሁ የምታስተምሩት ከድሃው ኢትዮጵያዊ ዘርፋችሁ መሆኑን እኛ እንድንነግራችሁ ትፈልጋላችሁን? የእናንተ ልጆች ተንደላቀው ሲማሩ ሌላው ኢትዮጵያዊ ግን ጎዳና ተዳዳሪ ሁኖ በድንቁርና ውስጥ እንዲኖር የፈረዳችሁበት መሆኑንስ አትገነዘቡምን? የዘመኑ ባለስልጣናት ለራሳችሁ ባለ ብዙ ፎቅ ቤቶችን  ሠርታችሁ ተንደላቃችሁ ስትኖሩ ከራሳችሁ የተረፈውንም በብዙ ሺህ ብር እያከራያችሁ ደስ ብሏችሁ ስትኖሩ ድሆች በላባቸው ጥረውና ግረው የሰሩትን ቤቶች አፍርሳችሁ ሜዳ ላይ መጣላችሁን ህዝቡ የማያይ ይመስላችኋልን ?እኛም ሆንን ሌሎች ሁሉንም እያየን እና እየሰማን ነው።ከህዝብ ተሰውሮ የሚቀር አንዳችም ነገር የለም።

እናንተ “እኔ” ብቻ ማለትን የምታውቁ ህወሃቶች ስሙ !!!

በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ እንዲህ እንደ እናንተ ዘመን ጎዳና ላይ የሚኖር ዜጋ ታይቶ አይታወቅም። እንዲህ አይነት ሁኔታ በጎሬቤት አገሮችም አልታየም። በሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎች በአገሪቷ ዋና ከተማ ጎዳና ላይ የሚኖሩት እናንተ እንመራታለን በምትሏት ኢትዮጵያ ብቻ ነው። ጭካኔያችሁ ወደር የሌለው በመሆኑና አገራዊ ስሜት በማጣታችሁ የአዲስ አበባ ጎዳናዎች በሺዎች በሚቆጠሩ ጎዳና ተዳዳሪዎች ሊሞሉ ችለዋል ።

“ኢትዮጵያን የምንስበር እኛ፤ የምንጠግንም እኛ” ብላችሁ በቅዥት የምትኖሩ ህወሃቶች አሁንም ስሙ!!!

መተማመኛችሁ ጠመንጃችሁ መሆኑን እናውቃለን። እናንተ ከጠመንጃ ወዲያ ማሰቢያ አካል እንደሌላችሁም ደህና አድርገን እንገነዘባለን። እኛ ግን እንዲህ እንላችኋለን ያ ስትግድሉት አልቅሶ ዝም ያላችሁ ህዝብ ሞትን የሚንቅበት ግዜ እሩቅ አይሆንም። ካሁን ወዲያ ምን ሊመጣ የሚልበት ግዜም እየመጣ ነው። ለዲኑ፤ ለሃይማኖቱ፤ ለነፃነቱ መሞት ክብርና ጀግንነት መሆኑን አምኖ የሚቀበልበት ግዜ ደርሷል።ያን ግዜ ያ የተሞረኮዛችሁት ጠመንጃ የሸንበቆ ምርኩዝ ሆኖ ተሰብሮ የሚወጋችሁ መሆኑን ልናሳውቃችሁ እንወዳለን። ያ ከመሆኑ በፊት ግን ከህዝብ ጎራ እንድትቀላቀሉ ሳንመክራችሁ አናልፍም።

ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ !!!

ግንቦት 7

No comments:

Post a Comment