Saturday, December 1, 2012

የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር ሰራዊት ወታደራዊ ጥቃት ፈፀመ


በሰሜን ጎንደር መተማ ልዩ ስሙ ዘባጭ ባህር በተሰኘ ስፍራ ህዳር 20-2005 ከወያኔው የመከላከያ ሰራዊት ቅጥረኛ ጋር የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር አገር አድን ሰራዊትEthiopian People Patriotic Front ባካሄደው ውጊያ 13 /አስራ ሶስት/ የእብሪተኛው ቡድን ታጣቂዎች በመግደልና 17 /አስራ ሰባት/ በማቁሰል እንዲሁም ተተኳሽ መሳሪያዎችን በመማረክ ከፍተኛ ድል ተቀዳጅቷል።
በእለቱ በተካሄደው ውጊያ የወያኔው ታጣቂ ኃይል ተጨማሪ ሰራዊት በአካባቢው ያዘመተ ሲሆን፡ አርበኛው ሰሞኑን በተከታታይ እየወሰደ የሚገኘው ድንገተኛ ወታደራዊ ማጥቃት እርምጃ የህዝቡን ትኩረት ከመሳቡም ባሻገር በኢትዮጵያውያን ዘንድ የፀረ-ወያኔ ትግል መነሳሳት አብይ ሚና እየተጫወተ መሆኑን  በርካቶች እየገለጹ መሆኑም እየተገለጸ ነው።
የፖለቲካ ትግል የመጨረሻ አማራጭ የሆነው የትጥቅ ትግልን መፍትሄ አድርጎ ለአመታት ያህል የጊዜ፣ የእውቀት፣ የጉልበት ብሎም የህይወት መስዋዕትነት እየከፈለ የሚገኘው የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር ኢትዮጵያን ከጎጠኛውና መሰሪው ኃይል የመከላከል አኩሪ ጥረቱን ዛሬም እንደ ትላንቱ ሳያሰልስ የሚገፋበት መሆኑን አስታውቋል።
ሰራዊቱ የተለመደውን ጀብድ በፈፀመበት አካባቢ የሚገኙ ነዋሪዎች የግንባሩን ሰራዊት እየተቀላቀሉ መሆኑን የገለጸው የድርጅቱ ወታደራዊ መምሪያ ግንባሩ በተከታታይ የወሰደውንና እየወሰደ የሚገኘውን  ወታደራዊ ማጥቃት የመላውን ኢትዮጵያ ህዝብ ድጋፍ የሚጠይቅ እንደመሆኑ መጠን ለሁለንተናዊ የአርበኝነት ትግሉ የተቻለውን በማበርከት ከስርዓት ለውጡ ተጠቃሚ የሚሆንበት አገር ለመገንባት መነሳት ይገባዋል የሚለውን መልዕክት  ያስተላለፋል።

No comments:

Post a Comment