Thursday, April 18, 2013

ሁሉም ለሀገሩ ዘብ ይቁም!!



writer and author from norway
በዘረኛው የወያኔ አገዛዝ በሀገራችን ዉስጥ የተጣለብን ከፋፍለህ ግዛ ዘመቻ ከቀድሞው በተለየ እጅግ ዘግናኝና አስከፊ በሆነ ሁኔታ ላይ መገኘት የሁሉንም ኢትዮጵያዊ ወኔና ሞራል ሳይነካ አይቀርም ብዬ እገምታለሁ።  ከዚህም ውስጥ ዋነኛውና የመጀመሪያው ሰሞኑን በአማራዉ ብሔረሰብ ላይ በመድረስ ላይ ያለው የዘር ማጥፋት ወንጀል ህዝቡን ከአድማስ አድማስ እያነጋገረው መምጣቱ ሲሆን፤ እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ለሀገሬ ምን ሠራሁ በማለት እራሱን እየጠየቀ ? ይህን ዘረኛ የሆነ የወያኔ መንግስት ከስር መሰረቱ ነቅሎ ለመጣል በቁርጠኝነት በመነሳት ሀገራዊ የዜግነት ግዴታውን መወጣት አለበት ፡፡ 


ለዚህም በዋንኛነት ትኩረት ተሰጥቶት ለነገ ይደር የማይባልበት ጉዳይ ፣ ማናቸውም የተቃዋሚ ፓርቲዎችና ፥ የድጋፍ ድርጅቶች ፣ አንድ በመሆንና እጅ ለእጅ በመያያዝ ቅድሚያ ለሀገር ሰጥቶ የመጣብንን የወያኔ ሰደድ እሳት ማጥፋት ግድ ይለናል ፡፡

ለዚሁም ለ- April 8 ቀን  በኦስሎ ኖርዌይ የዲሞክራሲ ለውጥ በኢትዮጵያና  ኢህአፖ የጠሩት ሀገርህን አድን ዘመቻ ጥሪ እንደ አንድ አብነት ሆኖ የሚጠቀስ  ነው ፡፡  ዘረኛው የወያኔ መንግስት ከጥነሰሱ ጀምሮ እስከአሁን ድረስ ስልጣን ላይ ፊጥ ብሎ እስከቀጠለበት ድረስ ሰንቆ ያመጣውን የሀይማኖትና የዘር ማጥፋት ትልም በተግባር ላይ ማዋል ከጀመረ እነሆ ብዙ አመታትን አስቆጥሯል ፡፡ ይኸውም የመጀመሪያው በሙስሊም ወገኖቻችን ላይ የተጀመረው የሀይማኖት ብጥብጥ በአይበገሬው የሙስሊም ወንድሞቻችን ትግል ዕለት በዕለት እየተፋፋመ ወያኔን እንቅልፍ ቢነሳውም ፣ ህወሃት-ኢሃዴግ ተስፋ ባለመቁረጥ እንደገና ፊቱን ወደ ኦርቶዶክስ ኃይማኖት በማዞር የተለመደውን የስልጣን ማራዘም ዘመቻና ህዝብን ከህዝብ የማፋጀት አባዜን በማፋፋም እነሆ አሁን ደግሞ የአማራውን ህዝብ ከእናት ምድሩና ሀገሩ የማባረርና ዘር የማጽዳት ዘመቻውን በሰፊው ተያይዞታል።

ይህም ከማናለብኝነትና ለህዝቡ ካለው ከፍተኛ ጥላቻና ንቀት የመነጨ በመሆኑና በአንድ ዘር የበላይነት ብቻ የማመን ጠባብነት ጭምር የተጸናወተው በመሆኑ ነው ። ወያኔ ከመጀመሪያው ጀምሮ በኢትዮጵያ አንድነት የማያምንና ጭራሽ ኢትዮጵያ የምትባል አገር እንደሌለችና ኢትዮጵያ የሚለውንም ስም ያገኘችው በሚኒሊክ ዘመነ መንግሥት መሆኑን ለማሳመን የሚያደርጉትን ባዶ ጥረት በመረጃ  አንድ ግለሰብ በኢሳት ቲቪ ላይ ከጋዜጠኛ ሲሳይ አገኔ ጋር ባደረገው ቃለ መጠይቅ ከነ መረጃቸው አስደምጦናል ። ይህም ማለት አማራው ለትግራይ ህዝብ ጠላቱ መሆኑን አስምረው አረጋግጠውልናል ማለት ነው ። እንደውም ለአማራ ያላቸውን ጥላቻና ዘረኝነት ለመግለጽ ሲሉ ! ሆስፒታል ውስጥ አንድ በሽተኛ ከፈረንጅ ሀኪምና ከአማራ ሀኪም ማን እንዲያክምህ ትፈልጋለህ ተብሎ ምርጫ ሲቀርብለት የመለሰው መልስ አማራ ከሚያክመኝ ፈረንጁ የፈለገውን ቢያደርገኝ ይሻለኛል ብሎ በሽተኛው እስከመመለስ መድረሱን አድምጠናል።

ጎበዝ ! ወያኔዎች እኮ ዛሬ አማራውን ነገ ደግሞ ጉራጌውን ከዛም ኦሮሞውን ከሀገር በማፈናቀል እንደተባለውም ኢትዮጵያ የተባለችውንና ለዘመናት ተከብራና ታፍራ የኖረችውን፤ ጀግኖች አባቶቻችን አጥንታቸውን ከስክሰው ደማቸውን አፍስሰው ያስረከቡንን ሀገር ከምድረ ገጽ ለማጥፋት ሆን ብለው የተነሱ አረሞች ናቸው።  እምነበረድ ይክበዳቸውና ! አሁን በአካለ ህይወት የሌሉት ፣ የቀድሞው ጠ.ሚኒስተር የነበሩት በራዕያቸው ግን አገሪቱን የሚያስተዳድሩት ሰው ባለቤት የሆንችው ወ\ሮ አዜብ መስፍን(ጎላ) ሰሞኑን በኢቲቪ ማቅ (ጥቁር ለብሳ)  እኛን ግን ሳቅ  አላብሳናለች ፣ ስለ ባለቤትዋ የወር ደሞዝ ማለት ነው ለኢህአዲግ መዋጮ ከፍሎ የሚደርሰው 4,000ብር ብቻ ነው ብላናለች ፡፡  አንድም ቀን ልጆቼን ፣ ቤቴን ሳይል ለሀገሩ 24 ሰአት ያገለገለ መሪ ነው ፥ ወደዚህ ሀገር ሲመጣም ጭንቅላቱን ብቻ ነው ይዞ የመጣው ብላናለች ። ሌላው ሰው ወደዚህ ዓለም ሲመጣ ምን ጨብጦ እነደመጣ ፣ ኧህ ! ካሏት አዜብ መስፈን ብዙ ቀልዶችን ሳትነግረን አትቀርም ፡፡

ወይዘሮዋን አንድ ያልገባት ነገር ቢኖር ፣  መለስ  ጭንቅላቱን አሟጦ የተጠቀመበት ፣ የባንዳ ልጅ እየተባለ ያደገበትን በቀል ፣ህዝቡ ላይ በመበቀል ሙሉ ኃይሉን የተጠቀመ  አረመኔ ፥ ጨካኝና ዘረኛ  መሪ መሆኑን ያለመረዳቷ ጉዳይ ነው ። ከዚህ በፊት የመለስ ራእይ ሳይደለዝና ሳይበረዝ ትግሉ ወደ ፊት ይቀጥላል ያልሽው እንደተጠበቀ ሆኖ ፣ ዛሬ ደሞ በትንሽ ደሞዝ እየተከፈለው ሌት ተቀን እየሰራ ሀገራችንን ትልቅ ደረጃ ላይ እንድትደርስ ያደረገ የመጀመሪያው መሪ መሆኑ ተሰምሮበት (Guinness book of records) ላይ ተመዝግቦ መቀመጥ አለበት አይነት ትእዛዛዊ የማስጠንቀቂያ መልክት በማስተላለፍ “የሌባ አይነ ደረቅ መልሶ ልብ ያድርቅ” አይነት ጨዋታሽን በጥሩ ተውኔታዊ ገቢር ! የሃዘን ልብስሽን እንደ ጉሬዛ ግንባርሽ ድረስ ተከናንበሽ ትውነሽልናል ፡፡

ምናልባት መለስ ዜናዊ ትግራይን አልምቶ ይሆናል አላውቅም በእርግጠኝነት ግን መናገር የምችለው ቀሪዋን ኢትዮጵያን አድምቷል ። ህዝቡንም እርስ በእርሱ ደም እንዲቀባባና ፥ በዘርና በሀይማኖት በመከፋፈል የሀገሪቷንም መሬት ለባእዳን በመሸጥ ህዝቡን ለከፍተኛ ችግርና መከራ አጋፍጦ ፣ ዜጋ ሁሉ የሚወዳትን ሀገሩን እየጣለ በየአረብ ሀገሩና አውሮፓ ውስጥ እንዲሰደድ ያደረገ ትልቅ የማይረሳ ነቀርሳና ጠባሳ ህዝቡ ላይ  ትቶ የሄደ መሪ ነው ። የእርሱን ራእይ በመከተል እነሆ አሁንም ያሉት መሪ ተብዬ ጃሌዎቹ ከሱ በባሰና አስከፊ በሆነ ሁኔታ ህዝቡን ከተወለደበትና እትብቱን ከቀበረበት ቀዬ በግፍና በጭቆና እያባረሩት ይገኛሉ ። ስለዚህ ጎበዝ ይህን ጉዳይ ዝም ብለን ማየት የማንችለውና ሁላችንም በአንድ ላይ ሆነን እጅ ለእጅ ተያይዘን ወያኔንና አንጃዎቹን “በቃ” ማለት የሚጠበቅብን ወቅቱ  ከምንግዜውም በላይ አሁን ነው ።

በመጨረሻም ማለት የምፈልገው ነገር ቢኖር የኢህአፓ ወክንድ የሚያደርገው እንቅስቃሴ እጅግ የሚያኮራ በመሆኑ ሳይደነቅ መታለፍ የሌለበት ጉዳይ ነው። ለዚሁም ከዚህ በፊት በሙስሊም ወገኖቻችን ላይ ወያኔ ያደረሰውን በደል አብሮ ከጎኑ በመሰለፍ ፣በኦርቶዶክስ ሀይማኖት ላይም እንዲሁ ችግሩን አብሮ በመጋፈጥና አሁን ደሞ በአማራው ህዝብ ላይ ወያኔ የሚያደርሰውን አሰቃቂ በደል በመቃወም በከፍተኛ እንቅስቃሴ ላይ ይገኛል። ሌላው ደግሞ ማናቸውም ለሀገራችን ተቆርቋሪዎች ነን የሚሉ ኢትዮጵያዊያኖች ወገኖቻችንን በሙሉ የሚያሳትፍ (keep of fighting ethiopian youth forum KOFEYF) የሚል የፓልቶክ (paltalk room) ከፍቶ ዘውትር በየሳምንቱ እሁድ ከ15፡00 – 3፡00pm ሰአት ጀምሮ አንጋፋ የሆኑ የፖለቲካ ባለሞያዎችንና የሀገር ተቆርቋሪዎችን በመጋበዝ ትልቅ አስተዋጾ በማድረግ ላይ ይገኛል ። እርሶም ይህን እድል በመጠቀም ያለዎትን እውቀት ለማህበረሰቡ በማስተማርና በመማር ለሀገርዎ  ትልቅ አስተዋጽኦ በማድረግ ዉድ ሀገራችንን  ኢትዮጵያን ከገባችበት የድጥ ማጥ ውስጥ እናውጣት የሚል ተማጽኖዬን በማክበር እጠይቃለሁ።

ኢትዮጲያ ለዘላለም ትኑር!!!

እግዚአብሔር አምላክ ኢትዮጵያ ሀገራችንን በምህረቱ ይጎብኛት!!!
Dawit Abebe, April 2013. Oslo

No comments:

Post a Comment