Sunday, September 23, 2012

በአስቸኳይ የተሰበሰበው የወያኔ ፓርላማ የሁለቱን አዳዲስ የወያኔ ሹመኞችን ምደባ ተቀብሎ የጠቅላይ ሚንስቴርነትና የምክትል ጠቅላይ ምንስቴርነትን ሥልጣን አጸደቀላቸው

የመለስ ዜናዊን ከዚህ አለም በሞት መለየት ተከትሎ እረፍት ላይ ከነበርበት ለሁለተኛ ጊዜ አስቸኳይ  ስብሰባ የተጠራው የወያኔ ፓርላማ በትናትናው ዕለት መስከረም 11 ቀን 2005 የሃይለማሪያም ደሳለኝን ጠቅላይ ምንስቴርነትና የደመቀ መኮንን ምክትል ጠቅላይ ምንስትርነት ማጽደቁን በአገዛዙ ሥር ያሉ መገናኛ ብዙሃን በሰፊው ዘግበዋል።

የወያኔ ፓርላማ አፈጉባኤ የሆነው አባዱላ ገመዳ ምላተ ጉባዔው መሟላቱን ጠቅሶ ለአስቸኳይ ስብሰባው የተያዘውን 3 አጀንዳዎች በቅደም ተከተል ሲያስተዋውቅ ሁለቱ የጠቅላይ ምንስትሩንና የምክትሉን ሹመት ማጽደቅ እንደሆነና  3ኛው  “የባንድራ ቀንን አስመልክቶ የቀረበውን ውሳኔ መመርመሮ ማጽደቅ “ የሚል መሆኑን ሲገልጽ ለአስቸኳይ ስብሰባ ተብሎ እረፍቱን አቋርጦ እንዲሰየም በተጠራው ስብሰባ ላይ በ 3ኛ አጀንዳ ነት የተያዘው ስለ ባንድራ ቀን መወያየት ምን አጣዳፊ እንዳደረገው ለአብዛኛው ተስብሳቢ ግራ እንደገባው ከምንጮች የተገኘው መረጃ አረጋግጦአል።

ከአንድ የተቃዋሚ መቀመጫ በስተቀር በፓርላማ ውስጥ ያሉትን መቀመጫዎች ሙሉ በሙሉ የተቆጣጠረው  ወያኔ ኢህአደግ የቀድሞ መሪዉን ለመተካት በጠራው በዚህ አስቸኳይ ስብሰባ መገኘት ከነበረባቸው 547 አባላቱ መካከል የተገኙት 375 ብቻ መሆናቸው የብዙ ፖለቲካ ገምጋሚዎችን ትኩረት ስቦ አልፎአል።

180 አባላት የሚገኙበት የኢህአደግ ምክር ቤት ባለፈው ቅዳሜ የግንባሩ ሊቀመንበርና ምክትል ሊቀመንበር አድርጎ የሰየማቸው ሃይለማሪያም ደሳለኝና ደመቀ መኮንን በትናትናው ዕለት በሸንጎው ጠቅላይ ምንስትርነትና ምክትል ጠቅላይ ምንስትርነት ሆነው ሲሾሙ በፓርላማው ውስጥ የነበረው የተሰብሳቢው ስሜት እጅግ ቀዝቃዛ ሆኖ ተስተውሎአል።

ሃይለማሪያም ደሳለኝ ቃለማሃላውን ከፈጸመ ቦኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ባደረገው ኦፍሴላዊ ንግግር ለዚህ ሥልጣን ያበቃውን ባለውለታውን መለስ ዜናዊን ደጋግሞ በየደቂቃው ሲያሞካሽና ሲያወድስ ከመሰማቱም በላይ በየትኛውም መንግሥታዊ የሥልጣን ርክክብ ወቅት ተሰምቶ በማይታወቅ አምልኮአዊ  ውዳሴ “ ዘላለማዊ ክብርና ሞገስ ለታላቁ መሪያችን ይሁን “ ሲል ተደምጦአል።

መለስ ዜናዊ ከዚህ አለም በሞት ከተለየ ወዲህ በኢህአደጎች እየተዘወተረ በመነገር ላይ ያለው “የመለስ ራ ዕይ አንተገብራለን ” መፈክር በትናትናው የሃይለማሪያም ደሳለኝና ምክትሉ ደመቀ መኮንን ንግግር ተደጋግሞ ተስተጋብቶአል። መለስ ዜናዊ በህይወት በነበረበት ወቅት ህዝባችንን ሲያምታታበትና ድፍን አለምን ሲያሞኝበት የኖረው በሃሰት ላይ የተመሰረተ የኢኮኒሚ ዕድገትን እንቀጥልበታለን ያለው ሃይለማሪያም ደሳለኝ ከሟቹ አለቃው ጉልበት በታች ሆኖ ሲጋት የኖረውን ሃሰተኛ የዕድገትና የልማት አሃዝ ሸምድዶ በአሥር አመት ውስጥ አገራችንን መካከለኛ ገቢ ካላቸው አገሮች ተርታ እናሰልፋለን ሲል መደመጡ ብዙዎችን አስገርሞአል።

የመለስ ዜናዊ አገዛዝ የዘረጋውን ዘረኝነትና አድሎአዊነት አገር ውስጥ ሆኖ በሰላማዊ መንገድ ለመታገል ባለመቻላቸው ለነጻነታቸው ሲሉ መሳሪያ ያነሱትንና በህዝባዊ አመጽ ለውጥ ለማምጣት የሚንቀሳቀሱትን አገር ወዳዶች እንደሌሎች የቀድሞ አለቆቹ ሁሉ በጠላት መሳሪያነት የፈረጀው ሃይለማሪያም ደሳለኝ አገሪቱ ውስጥ የዲሞክራሲና የሰብአዊ መብት ተቋማት ግንባት በመልካም ጅምር ላይ ያለ በማስመሰል እንገፋበታለን  ሲል ተደምጦአል።

ሃይለማሪያም ደሳለኝም ሆነ በትናትናው ዕለት አስቸኳይ ስብሰባ የደረገው የወያኔ ፓርላማ የአገሪቱን መጻይ ዕድል ሊወስን ስለሚችለው ሁሉ አቀፍ የፖለቲካ ድርድር ያሉት አንድም ነገር አልነበረም። በዚህም ምክንያት የሃይለማሪያም ደሳለኝ ካቢኔ ገና ከጅምሩ “የጉልቻ ቢለዋወጥ” አይነት መሆኑን ይፋ በማድረጉ ሥልጣን ላይ ምን ያህል ዕድሜ ሊኖረው እንደሚችል የሚወስነው ኢትዮጵያዊያን ለነጻነታችንና ለክብራችን የምናደርገው ወሳኝ ትግል እንደሆነ ሁሉም ይስማማበታል።

No comments:

Post a Comment