Thursday, October 25, 2012

ጤና ጥበቃ ከታራሚዎች 62 በመቶዎቹ በአዕምሮ ጭንቀት በሽታ የሚሰቃዩ ናቸው አለ

:-የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ሰሞኑን ብሔራዊ የአዕምሮ ጤና ስትራቴጂን ይፋ ባደረገበት ወቅት በለቀቀው መረጃ፤ በአዲስ አበባ፣ በቃሊቲና በተለያዩ ማረሚያ ቤቶች ከሚገኙት ታራሚዎች መካከል 61 ነጥብ 9 በመቶ የሚሆኑት በከፍተኛ የአዕምሮ ጭንቀት የተጠቁ መሆናቸውን ያመለክታል።
ታራሚዎቹን ለአዕምሮ ጭንቀት ከሚዳርጓቸው ምክንያቶች መካከል በጠባብ ክፍል ውስጥ መታፈግ፣ በግዳጅ ለብቻ እንዲገለሉ ማድረግ ፣ብዙም እንቅስቃሴ አለማድረግ፣ በቀጣይ ህይወት ላይ ተስፋቢስ መሆን፣ ከለመዱት ማኅበራዊ ህይወት መለየት፣ በቂ የሆነ የጤና አገልግሎትን በተለይም የአዕምሮ ጤንነተን የሚመለከት አገልግሎት በማረሚያ ቤቶቹ አለማግኘት በዋነኝነት ተጠቅሰዋል።

በማረሚያ ቤቶች ታራሚዎች ራሳቸውን የሚያጠፉበት ሁኔታ መኖሩን የገለፀው ይሄው መረጃ፤ ከተጠቀሱት ችግሮች ጋር በተያያዘ ታራሚዎች በድብርት (Depression) ውስጥ ይገባሉ ብሏል።

የእያንዳንዱን ታራሚ የአዕምሮ ችግር ለመፈተሽና ተጠቂዎቹን ለመከታተል የአቅም ውስንነት ያለ መሆኑን የገለፀው ይሄው የጤና ስትራቴጂ፤ በተመሳሳይ መልኩ ችግሩንም ለማቃለል የአቅም ውስንነት መኖሩን አስቀምጧል።

ዘላቂ መፍትሄ ለማፈላለግም የፌዴራሉ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር መስሪያ ቤት ከፍትህ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤት ጋር በመተባበር በቀጣይ በጋራ የሚሰራ መሆኑን አስታውቋል።

በዚህም ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ በቀጣይ በፍትህ ሥርዓቱ ውስጥ የሚያልፉትንና እስር ቤት ውስጥ ያሉት ታራሚዎችን የአዕምሮ ጤንነትን ለመከታተል የሚያስችለውን የመግባቢያ ስምምነት ከፍትህ ሚኒስቴር ጋር ለመፈራረም ሰነድ እያዘጋጀ መሆኑን የሰንደቅ ዘገባ ያመለክታል።

No comments:

Post a Comment