Friday, November 15, 2013

Ethiopian police brutally beat, arrest demonstrators at the Saudi Embassy (Text+Video)

በሳውዲ ኢምባሲ የተጠራው የተቃውሞ ሰልፍ በፖሊስ ተበተነ፤ ከቀናት በፊት ከሳውዲ የተመለሰች ወጣት በሰልፉ ድብደባ ደርሶባታል
15 የፓርቲው አመራሮች ታስረዋል
አውራምባ ታይምስ (አዲስ አበባ) – በቅርቡ የሳውዲ አረቢያ መንግስት በንጹሀን ኢትዮጵያዊያን ላይ የፈጸመውን ኢ-ሰብአዊና እንስሳዊና ድርጊት በመቃወም ሰማያዊ ፓርቲ የጠራው ሰላማዊ ሰልፍ፤ ፖሊስ በወሰደው የኃይል እርምጃ ተበተነ፡፡
ዛሬ አርብ፣ ህዳር 6 ቀን 2006 ዓ.ም ከጠዋቱ 5፡00 ሰዓት በተለምዶ ወሎ ሰፈር ተብሎ በሚጠራው ስፍራ ከአይቤክስ ሆቴል ፊለፊት በሚገኘው የሳውዲ አረቢያ ኢምባሲ ደጃፍ የተጠራው ሰላማዊ ሰልፍ የፓርቲው አባላትና አመራሮች እንዲሁም ጋዜጠኞችና ከቀናት በፊት ከሳውዲ አረቢያ የተመለሱ ዜጎች የተሳተፉበት ነበር፡፡ ሆኖም ሰልፉ ለጥቂት ደቂቃዎች ከተካሄደ በኋላ ፖሊስ ሰልፈኞቹን ለመበተን በወሰደው የሃይል እርምጃ በተወሰኑ ሰልፈኞች ላይ የአካል ጉዳት ደርሷል፡፡ በስፍራው የተገኘው የአውራምባ ታይምስ ዘጋቢም የፖሊስ ዱላ ከመቅምስ አላመለጠም፡፡demo
ፖሊስ ክፉኛ ከደበደባቸው ሰልፈኞች መካከል በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ድጋፍ ባለፈው ረቡዕ ወደ አገራቸው የተመለሱ ዜጎች ይገኙበታል፡፡ ከትናንት በስቲያ ወደ አገሯ መመለሷን ለአውራምባ ታይምስ የገለጸች አንድ ወጣት እንደገለጸችው ‹‹ሌሎች ያደረሱብ በደል አንሶ፤ በራሳችን ወገን በገዛ አገራችን እንዴት እንዲህ አይነት ድብደባ ይፈጸምብናል›› ብላለች፡፡
ሌላው ከሳውዲ የተመለሰ አንድ አስተያየት ሰጪ በበኩሉ ‹‹እንኳን እዚህ እዛም የጭካኔ እርምጃቸውን ተቋቁመን በድፍረት ሰልፍ አካሂደናል፤ በአገራችን እንዴት ሰልፍ እንከላከላለን›› ሲል በግርምት ተናግሯል፡፡
ለአውራምባ ታይምስ ዘግይቶ በደረሰ መረጃ መሰረት የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር የሆኑት ኢ/ር ይልቃል ጌትነትን ጨምሮ 15 አመራሮችና አባላት ከሰልፉ ጋር በተያያዘ ለእስር ተዳርገዋል፡፡
በጉዳዩ ላይ አስተያየት እንዲሰጡ ጥያቄ ያቀረብንላቸው የመንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት ም/ኃላፊ አቶ ሽመልስ ከማል ሰልፉ ፍቃድ ያልተሰጠው ህገወጥ ሰልፍ ነው ካሉ በኋላ ስለ ሰላማዊ ሰልፍ በተደነገገው አዋጅ ላይ ማንኛውም ሰልፍ ከእምነት ተቋማትና ኢምባሲዎች በ500 ሜትር ርቀት ላይ መካሄድ አለበት የሚለውን የአዋጁ ክፍል በመጣስ ህዝብና ህዝብ ሊያጋጩ የሚችሉ የጸረ-አረብ ስሜት የሚንጸባረቅባቸው ዘረኛ መፈክሮች በዚህ ህገወጥ ሰልፍ ሲስተጋቡ ፖሊስ ዝም ማለት አልነበረበትም፡፡ እርምጃውም ተገቢ ነበር ብለዋል፡፡
የፋሺሽት መፈክር አንግቦ በተጎሳቆሉ ዜጎች ስም የፖሊቲካ ትርፍ ለማግኘት መጣር ብሎም መንግስት በዜጎቹ ግዴለሽ እንደሆነ አስመስሎ ማቅረብ ኃላፊነት ይሰማኛል ከሚል የፖሊቲካ ድርጅት አይጠበቅም፤ ያሉት አቶ ሽመልስ ‹‹የሳውዲ መንግስት በአገሩ የአሰሪና ሰራተኛ ህግ መሰረት እርምጃ የመውሰድ ሉአላዊ መብት እንዳለው እንገነዘባለን፤ እኛ ደግሞ የሚመለሱ ዜጎቻችንን በአገራቸው አምራችና ስራ ፈጣሪ እንዲሆኑ በዘላቂነት ለማቋቋም በአገር ደረጃ ብሄራዊ ኮሚቴ አዋቅረን ስራ እየሰራን ነው፡፡›› ብለዋል


No comments:

Post a Comment