Tuesday, February 18, 2014

ረዳት ፓይለት ሃይለመድህን ተላልፎ ይሰጣል የሚል እምነት የለኝም።


ከፋሲል የኔአለም (ጋዜጠኛ)
Feb 18.2014

አንደኛ፣ ኢትዮጵያ የሞት ቅጣትን ተግባራዊ የምታደርግ አገር ናት። 
ሁለተኛ፣ ኢትዮጵያ በሰብአዊ መብት ጥሰት በአለም የምትታወቅ ናት።
ሶስተኛ፣ ኢትዮጵያና ስዊዘርላንድ ተጠርጣሪዎችን አሳልፎ የመስጠት ስምምነት ( extradition treaty) የላቸውም::
አራተኛ፣አለማቀፍ የሰብአዊ መብት ድርጅቶችና በአውሮፓ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ዝም ብለው አይቀመጡም።

አምስተኛ፣ እንደሚባለው ጭንቀት ኖሮበት ድርጊቱን ከፈጸመም የበለጠ ወደ ኢትዮጵያ እንዳይመለስ ያደርገዋል። ምክንያቱም በስደተኝነት ህግ የአእምሮ ጭንቀት ያለባቸው ሰዎች ጥገኝነት ለማግኘት ከፍተኛ እድል አላቸውና።
ስድስት፣ የአእምሮ ጭንቀቱ መንስኤ የቅርብና ከአጎቱ ሞት ጋር በተያያዘ ከሆነ ደግሞ ጥገኝነት ለመጠየቅ ጉዳዩን ይበልጥ ያከብድለታል ምክንያቱም የአጎቱ ሞት መንስኤ እስካሁን እንቆቅልሽ እንደሆነ አለና። እህቱ የጻፈችውም ደብዳቤ የሃይለመድህንን ችግር ይበልጥ የሚያሳይ ነው ። "ጠላቶች እንዳሉ እንደሚያምን ፣ ስልኩን እንደጠለፉት እንደሚያስብ፤ በላፕቶፑ ካሜራ ሳይቀር ያዩኛል ብሎ ስለሚሰጋ ካሜራውን ሳይሸፍን እንደማይከፍት እንዲሁም፤ ወጥቶ እስኪገባ ቤቱን ሲበረብሩ የቆዩ ስለሚመስለው ካሜራ ጠምዶ መሄድ " መጀመሩን መግለጿ፣ የሃይለመድህ መሰረታዊ ችግር የደህንነት ዋስትና ማጣት መሆኑ በአገሪቱ ውስጥ ያለውን የደህንነት እጦት (insecurity) የሚያሳይ ነው። በቤተሰቡ በተለይም በአባቱ ላይ ተከፍቶ የነበረው የማጥፋት ዘመቻም ለጭንቀቱ መንስኤ ሊሆን ይችላል።

የሃይለመድህን ድርጊት ባለሁለት ሰይፍ ነው። የኢትዮጵያ መንግስት በሁለቱም ሰይፍ መቆረጡ አይቀርም። ፓይለቱን የአእምሮ በሽተኛ አድርጎ ቢያቀርበው፣ ለአየር መንገዱ ትልቅ ኪሳራ ነው። መንገደኞች ከእንግዲህ በኢትዮጵያ አየር መንገድ ለመጓዝ ድፍረቱ አይኖራቸውም፣ ለዚህም ይመስለኛል አቶ ሬድዋን ፓይለቱ ሙሉ ጤነኛ ነው ሲሉ መግለጫ የሰጡት። ወጣቱ ለስደት መጠየቂያ በማሰብ የወሰደው እርምጃ ነው ቢሉም፣ " በደህና የኑሮ ሁኔታ ላይ የሚገኝ ሰው እንዴት ስደትን ሊመርጥ ቻለ?"፣ ከስደት የከፋ ችግር ቢያጋጥመው ነው ተብሎ የኢትዮጵያ የሰብአዊ መብቶች አያያዝ መነሳቱ አይቀሬ ነው። መንግስት ግራ ሲጋባ ይታየኛል።
             
                     

No comments:

Post a Comment