Tuesday, April 2, 2013

በአማራ ተወላጆች ላይ የተፈጸመው የዘር ማጥራት ወንጀል ሊያስጠይቅ እንደሚችል አንድ ታዋቂ ምሁር ገለጹ


መጋቢት ፳፬ (ሀያ አራት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-በተባበሩት መንግስታት ድርጅት አማካኝነት በሩዋንዳ የተካሄደውን የዘር ማጥፋት ወንጀል በአቃቢህግነት በመምራት  የሚታወቁት የህግ ባለሙያው ዶ/ር ያዕቆብ ሀይለማርያም ከኢሳት ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ እንደገለጡት ከዚህ ቀደም በደቡብ ክልል በጉራፈርዳ ወረዳ፣ አሁን ደግሞ በቤንሻንጉል ጉሙዝ በአማራ ተወላጆች ላይ እየተፈጸመ ያለው ወንጀል በማንኛውም ጊዜ ሊነሳ የሚችል ዘር ማጥራት ወንጀል መሆኑን ገልጸዋል።
ምሁሩ እንዳሉት ድርጊቱ የዘር ማጥፋት ወንጀል ባይሆን እንኳ የዘር ማጥራት ወንጀል በመሆኑ በይርጋ የማይታገድ በማንኛውም ጊዜ በአለማቀፍም በኢትዮጵያም ህግ የሚያስጠይቅ በመሆኑ በስልጣን ላይ ያሉት ሰዎች ቆም ብለው ሊያስቡበት እንደሚገባ መክረዋል። በውጭም ሆነ በአገር ውስጥ ያሉ ኢትዮጵያውያን ተጨባጭ ማስረጃዎችን በመያዝ ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት ቢያቀርቡት ድርጊቱን የፈጸሙትን ለህግ ማቅርብ እንደሚቻልም ዶ/ር ያእቆብ ገልጸዋል
የቤንሻንጉል ጉሙዝ ባለስልጣናት ቀደም ብሎ ደግሞ ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ሰዎቹ የሚባረሩት አማራ ስለሆኑ ሳይሆን ደን ስለሚጨፈጭፉ ነው በማለት የተሰጠው ምክንያት ተገቢ አለመሆኑን የገለጡት ዶ/ር ያእቆብ ፣ ደን የጨፈጨፉ ካሉ በህግ ይጠየቃሉ እንጅ ወደ ክልላችሁ ሂዱ ሊባሉ አይገባም ብለዋል። ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ይህን ድርጊት ማውገዝ እንደሚገባውም ምሁሩ ገልጸዋል ።
ሁሉም የኢትዮጵያ ባለስልጣናት ተጠያቂ መሆናቸውን የገለጡት ምሁሩ፣ በመንግስት በኩል የሚቀርበው መከራከሪያ ፈጽሞ ተቀባይነት የለም ሲሉ በአጽኖት ገልጸዋል።
ዶ/ር ያእቆብ ድርጊቱ ስሜታቸውን እንደጎዳው አልሸሸጉም።
በተመሳሳይ ዜና ደግሞ በማህበራዊ ድረገጾች ጽሁፎችን በመጻፍ የሚታወቁት መምህር አብረሀ ደስታ ” የአማራ ተፈናቃዮች በህወሀት ተግባር ምክንያት በትግራይ ህዝብ ቅር ሊሰኙ ይችላሉ። እንዲህ ከሆነ ደግሞ ዛሬ በአማራ ህዝብ እየተፈጸመ ያለው ግፍ ነገ በትግራይ ህዝብ መደረጉ አይቀርም። ግለሰቦች በስልጣን ለማቆየት ሲባል በሰለማዊ ንጹህ ዜጎች ግፍ እየተፈጸመ ዝም ብሎ መመልከት ተገቢ አይደለም።” ካለ በሁዋላ ፣ ይህ የማፈናቀሉ ተግባር ካልቆመ መጨረሻው ምን ሊሆን ነው? ስለሌሎች ስናስብ ስለራሳችን እአሰብን ነው።” ብለዋል።

No comments:

Post a Comment