Monday, December 30, 2013

በጀግኖች አባቶቻችን ደም የተቦካው ሉአላዊ ግዛታችን ላይ የሚደረገውን ስውር ሴራ ያለማወላወል በፅናት እንታገለዋለን፡፡ ከሰማያዊ ፓርቲ (ሰማያዊ) የተሰጠ መግለጫ

 
ታኅሣሥ 20 ቀን 2006 ዓ.ም. (December 30, 2013) 
የኢትዮጵያንና የሱዳንን ድንበር የማካለሉ ሥራ ከመስከረም 29 ቀን 2002 ዓ.ም. (October 9, 2009) ጀምሮ እየተከናወነ እንደሆነ፣ በእንግሊዘኛ ቋንቋ የሚታተመው ዕለታዊ የሱዳን ጋዜጣ ሱዳን ትሪቢውን (Sudan Tribune) በመስከረም 8 ቀን 2002 ዓ.ም. (September 18, 2009) መዘገቡ ይታወሳል፡፡ የኢትዮጵያና የሱዳን የድንበር ጉዳይ ያንገበገባቸው ኢትዮጵያውያን በሀገር ውስጥና በውጪ የሚኖሩት ዜጎቻችንም ራሳቸውን በተለያዩ “ኮሚቴዎች” እና “ግብረ ሃይሎች” በማደራጀት ለጉዳዩ ክፈተኛ ትኩረት እንዲሰጠው ሲጥሩ ቆይተዋል፡፡ ፓርቲያችን (ሰማያዊ)፣ ለነዚህ ሀገር ወዳድ ዜጎች ያለውን ከፍተኛ አክብሮት ለመግለጽ ይወዳል፡፡ 

ሆኖም፣ የነዚህን ሀገር ወዳድ ዜጎችና አፍቃሪ-ኢትዮጵያውያን ጥሪና መግለጫዎች ከቁብም ካለመቁጠር፣ በሥልጣን ላይ ያለው የወያኔ-ኢህአዲግ መንግሥት ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጀርባ ሥውር የሥልጣን ማራዘሚያ ደባዎችን እየሸረበ እንደሚገኝ አጋልጠዋል። ወያኔ ራሱ ያቋቋመው “የኢትዮጵያና የሱዳን ድንበር ኮሚቴ” አባላት ራሳቸው በተለያዩ ቃለ-ምልልሶች እንዳጋለጡት፣ ወያኔ በአባቶቻችን ደም ተላቁጦ ለተቦካውና የበርካታ ሰማዕታትን ህይወት ላስከፈለው የኢትዮጵያ ድንበርና የግዛት ሉዓላዊነት ግዴለሽነቱን በተግባር አሳይቷል፡፡ የኢትዮጵያንም ሉዓላዊ ግዛትና ድንበር “በጫካ ውሎችና ስምምነቶች” እያመካኘ ለኢትዮጵያና ለኢትዮጵያውያን ታሪካዊ ጠላቶች አሳልፎ መስጠቱን አጠናክሮ ቀጥሎበታል፡፡ 

ይህንንም ከፍተኛ የሆነ የሃገር ክህደትና ኃላፊነት የጎደለው ተግባር ለማስተባበል በመገንዘብ፣ የወያኔ-ኢህአዲግ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በድረ-ገጹ ላይ በመስከረም 2002 ዓ.ም መጨረሻ ላይ አንድ የማደናገሪያ መግለጫ አውጥቶ ነበር። ከዚህም የማደናገሪያ መግለጫ ውስጥ የሚከተሉትን ሦስት(3) አበይት ጉዳዮች መገንዘብ ይቻላል። እነርሱም፦ 

1ኛ. የኢትዮጵያና ሱዳን የፖለቲካ ኮሚቴ (Ethio-Sudan Political Committee) ተብሎ የሚጠራ ከፍተኛ አካል መኖሩንና የኢትዮጵያና የሱዳን የጋራ ድንበር ኮሚቴም (Ethio-Sudan Joint Boundary Committee) በፖለቲካው ኮሚቴ ሥር እንደሚሠራ አረጋግጧል፤ የዚህ የኮሚቴ መዋቀርና የአሰራር ሂደቱም ለረጅም ዓመታት ከኢትዮጵያ ሕዝብ አይንና ተደብቆ የቆየ እንደሆነና፣ ወያኔ-ኢህአዲግም በሀገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን ክትትል መጋለጡን ሲያውቅ ተጨንቆ ያወጣው ምስጢር ነበር። 

2ኛ. የኢትዮጵያና የሱዳን የጋራ የድንበር ኮሚቴም (Ethio-Sudan Joint Boundary Committee) ከጥቅምት 5 ቀን 2002 ዓ.ም. (October 15, 2009) እስከ ግንቦት 2002 ዓ.ም.(May 2010) ድረስ የኢትዮጵያና ሱዳን ድንበርንና አካባቢውን ሙሉ በሙሉ እንደሚቀይስና ቅኝት እንደሚያደርግም ገልጾ ነበር፡፡ ይህ ደግሞ ወያኔ ሲጋለጥ ያወጣው ሌላው ምስጢር ሲሆን፣ (ሱዳን ትሪቢውን ያወጣውን ዜና የሚያጎለምስ) እና የሱዳን ሃገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስቴር ድንበሩን ለማካለል የሚያደርገውን ዝግጅት የሚያስተጋባ ነው። 

3ኛ. የድንበር ክለላው ከግንቦት 2002 ዓ.ም. ( May 2010) በኋላ እንደሚደረግና ከዚህም ጋር አያይዞ ወያኔ-ኢህአዲግ ያለፉት የኢትዮጵያ መንግሥታት አምነው የተቀበሉት የድንበር ክልል እንዳለ አስምስሎ ለማቅረብም ጥረት አድርጎ ነበር፡፡ በመሆኑም፣ ወያኔ-ኢህአዲግ አሁን የሚያካሂደው “የድንበር-ክለላ ሂደት” ዳግም ድንበርን የመከለል ተግባር ( re-demarcation ) እንደሆነ መግለጹ ለመግለጽ ሞክረዋል፡፡ ይህ ማደናገሪያና ተራ ልፈፋ፤ የኢትዮጵያን ህዝብ ለማወናበድና ግዛቱን በጫካ ውሎችና ስምምነቶች አማካይነት አሳልፎ ከመስጠት የዘለለ ኢምንት እውነታ የለውም፡፡ ይሄንን በተመለከተም ያጠኑት ሊቃውንትንና በግዛቱ ላይ የሚኖሩትን ዜጎች ምስክርነት ሊያገኝ አልቻለም፤ አይችልምም፡፡

የወያኔ-ኢህአዲግ መንግሥት “ያለፉት የኢትዮጵያ መንግሥታት የተቀበሉት የድንበር ክልል” የሚለው ሀተታ፤ ሜጀር (ሻለቃ) ጉዊን የተባለው የእንግሊዝ ጦር መኮንን በ1902 ዓ.ም. (እ.አ.አ.) “አስምሬአለሁ” የሚለውን የወሰን ክልል ነው። ይሁንና አንድ በእንግሊዝ የቅኝ-ገዥነት አባዜ የሰከረ ሻለቃ ያሰመረውን መስመር መሠረት አድርጎ ፀረ-ኢትዮጵያና ፀረ-ሉዓላዊነትን የወያኔ-ኢህአዲግ ገዢ ቡድን “ለሱዳን ይገባታል” ብሎ መሟገቱ የፖለቲካ ቅጥፈት እንጂ ታሪካዊ ማስረጃ የለውም፡፡ የሚከተሉትም ታሪካዊ ዳራዎች የወያኔን ሙግት ውድቅ ያደርጉታል፦

1ኛ.ሻለቃ ጉዊን መሬቱን አካልያለሁ ሲልና በወረቀት ሲያሰምር፤ በኢትዮጵያ በኩል አንድም ተወካይ ስለአልነበረ የጉዊን የድንበር ማካለል ተግባር ከቅኝ ገዢዎች ማንአለብኝነት ተለይቶ የማይታይና የውል አፈጻጸም ሥርዓት የማይከተል በመሆኑ የተነሳ ተቀባይነት የለውም፡፡

2ኛ. የ1896 ዓ.ም.(እ.አ.አ.) የአድዋ ጦርነት ድል በቅኝ ገዥዎች ላይ በፈጠረው ከፍተኛ መደናገጥ ምክንያት 1902 ዓ.ም. (እ.አ.አ.) አካባቢ እንግሊዝና ጣሊያን በጋራ በመመሳጠር የሰሜንና የምዕራብ ኢትዮጵያን ድንበር ለመግፋት የፈፀሙት ሴራ ስለሆነ፣ የሻለቃ ጉዊን ተልዕኮም ከዚያ ሴራ ተነጥሎ ሊታይ አይችልም፡፡ ስለሆነም ተቀባይነት የለውም፡፡

3ኛ. ከአፄ ምኒልክ ዘመነ መንግሥት በፊትም ይሁን ከዚያ በኋላ፣ ይህ ሻለቃ ጉዊን ከለለው የሚባለው መሬት ምን ጊዜም ቢሆን ከኢትዮጵያ ይዞታ ውጭ ሆኖ አያውቅም፡፡ ይባስ ብሎም፣ በአፄ ቴዎድሮስና በአፄ ዮሐንስ ዘመነ መንግሥት የኢትዮጵያ ግዛት አሁን ሱዳን ተብሎ ከሚጠራው ሃገር በጣም ወደ ውስጥ የገባ ነበር፡፡ ስለሆነም፣ የግዛት ጥያቄ ሲነሳ የይገባኛል ታሪካዊ መሠረት ያላት ኢትዮጵያ መሆኗን ለማስተባበል አዳጋች ነው፡፡ 

4.አሁን የወያኔ-ኢህአዲግ መንግሥት በመጋቢት 22/2006 ዓ.ም ገደማ March 30, 2014 ለሱዳን ለመስጠት ቅድመ-ዝግጅቱን አጠናቋል፡፡ ለኢትዮጵያ ህዝብ ከፍተኛ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ምንም አይነት ግልጽነትና ተጠያቂነትን መርሆው ያላደረገው የወያኔ-ኢህአዲግ መንግሥት ግን አንዳችም መረጃ የኢትዮጵያ ህዝብ እንዳያገኝ የተለመደ አፈናውን ገፍቶበታል፡፡ በመሆኑም፣ በእልፍ-አዕላፍ ድንበር ጠባቂ ኢትዮጵያዊያን ደምና አጥንት ተጠብቆ የኖረውን ዳር ድንበር፣ ወያኔ በተለመደ “የደጃዝማቾች ፈረስ መጠጫና ጉግዝ መጫወቻ ነው” በሚል ንፍገት አሳልፎ ለሱዳን ሊሰጠው ተዘጋጅቷል፡፡ ይህ የምዕራብና የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሰፊ ውሃ-ገብና ለም ሉዓላዊ መሬት፣ የታሪክ ማስረጃዎችንና የኢትዮጵያውያንን መስዋዕትነት በማናናቅ ለባዕዳን ሊሠጥ አይችልም፡፡ 

ስለዚህ ከላይ በተጠቀሱት ማስረጃዎችና በዓለም-አቀፍ የአሠራር ደንብ መሠረት፤ ወያኔ-ኢህአዲግ ከሱዳን ጋር የሚያደርገው የድንበር ክለላ ስምምነት ህገ-ወጥ ነው። ከዚህም ባሻገር፤ ከዋናው ባለጉዳይ የኢትዮጵያ ሕዝብ በስተጀርባ የሚደረግ ማንኛውም ዓይነት ስምምነት ይሁን የድንበር ክለላ ተግባር ምንም ዓይነት ተቀባይነት አይኖረውም። 

ከዚህም ሌላ፣ ወያኔ-ኢህአዲግ የተወሰኑ የኢትዮጵያን ሉዓላዊ መሬት ቆርሶ በመስጠት ሥልጣኑን በጎረቤት አገር ሱዳን ለማስባረክ ብሎ የሚያደርገው ሽር-ጉድ በየትኛውም መስፈርት ተቀባይነት የለውም፡፡ ውጤቱም “ታግዬላቸዋለሁ የሚላቸውን ብሄሮችና ብሔረሰቦች” ከማዳከምና ብሎም ለማፈራረስ የተጠቀመበተ ዘዴ የቅኝ ገዢዎች ለራሳቸው ጥቅም ማስጠበቂያ ያሰመሩትን የድንበር መስመር በመቀበልና የቅኝ ገዢ ጠበብትን እንደ ምስክር በመጠቀም ነው። ይህም ተግባሩ፣ቀድሞውንም በቋፍ የነበረውን የወያኔ-ኢህአዲግን መንግሥት የፖለቲካ ቅቡልነት የሚያሳጣው መሆኑን ለማስታወስ እንፈልጋለን፡፡ አልፎ-ተርፎም በዚህ ተግባሩም ዛሬም የቅጥረኛ ሥራ እያከናወነ እንደሆነ ህዝቡ እንዲያውቀው እንፈልጋለን፡፡

ይህ የወያኔ-ኢህአዲግ ገዢ ቡድን ተግባር የሃገራችን ኢትዮጵያን ዓለም-አቀፍአዊ ክብር የሚጎዳ ስለሆነ ከተግባሩ እንዲታቀብ እናሳስባለን፡፡ በተጨማሪም፣ ለጉዳዩ ባለቤት ለሆነው ለኢትዮጵያ ህዝብ፣ ዝርዝር መረጃና ያለውን ተጨባጭ ሁኔታ የማሳወቅ ግዴታ እንዳለበትም ልንገልጽ እንወዳለን፡፡ ይህን ሳያደርግ ቢቀር ግን፣ ፓርቲያችን የተጣለበትን የአባቶቻችንን ክብርና የሀገራችንን ሉዓላዊነት የማስጠበቅ ታሪካዊ ኃላፊነት መቼም ቢሆን ያለምንም ማወላወል የምንወጣ መሆናችንን ለጉዳዩ ባለቤት ለኢትዮጵያ ኅዝብ በድጋሚ እናረጋግጣለን፡፡

ሰላም፣ ተስፋ፣ ፍትህና እኩልነት በዲሞክራሲያዊና ሰብዓዊ መብቶች በተከበሩባት ኢትዮጵያ ዕውን ይሆናል!!!

Saturday, December 28, 2013

ፍትህ የተጠማች ብላቴና



በአንድነት ጠቅላላ ጉባኤ ወቅት ታዳጊዋ ፍትህን ጠየቀች (ከፍኖተ ነጻነት የተወሰደ)

«ይህች ህጻን አማራም፣ኦሮሞም፣ጉራጌም፣ትግሬም ፣ሙስሊም፣ክርስቲያን ፣የኢህአዴግ ተቃዋሚ ወይም ደጋፊ ፣ሽፍታ አይደለችም፡፡ለሁሉም ያልደረሰች ህጻን ብቻ ናት፡፡ሁላችንንም የምትጠይቀን ፍትህ ብቻ ነው፡፡አባቷን ገድለው እጇን በጥይት ቆርጠዋል፡፡ምናልባት ሳድግ መምህር የመሆን ህልም አለኝ ብላኛለች፡፡ማን ነው ለዚህ ህልሟ የሚያደርሳት ?ወዳጄ ነገ ከነገ ወዲያ በአዲስ አበባ በአንድ ቦታ ሳንቲም ትሎት ወይም ትለን ይሆናል፡፡እውን ህመሟ ይሰማናል?ይሰማቸዋል?» ሲል ነበር የአንድነት ጥቅላላ ጉባኤ ተካፋይ አባቷን እንዲሁም እጆቿን ያጣችዉን ታዳጊ ወጣት ሲያስተዋወቅ የተነገሩት።

አባቷን በጥይት የተነጠቀችውና እጇን የተቆረጠችው ታዳጊ በጠቅላላ ጉባኤው በቀረበበችበት ወቅትም ፣ አባላቱ በእንባ ታጥበዋል፣ቁጭት ውስጣቸውን አንገብግቦት ‹‹ፍትህ፣ፍትህ፣ፍትህ» በማለት ጩኅታቸውን አሰምተዋል።

አባቷ ለበርካታ አመታት የኢሕአዴግ /ብሃዴን አባል የነበሩ፣ መዋጮ የሚያዋጡ ሰው ነበሩ።ሰባት ልጆች የነበሯቸው ሲሆን በዚህ ሁኔታ ሕይወታቸው ማለፉ የአገዛዙን ምንነት ብዉ አደርጎ ያጎላ ነዉ።

ቪዲዮዉን ይመልከቱና ይፍረዱ !





Esat special Public meeting in Bergen Norway part 1 and 2 Dec14 2013

በኖርዌ በርገን ከተማ በዲሞክራሲያዌ ለውጥ ድጋፍ ድርጅት በኖርዌ አዘጋጅነት  የተደረገ ህዝባዊ  ስብሰባ




Wednesday, December 18, 2013

የግንቦት7 ህዝባዊ ሀይል “መጪው አመት ህዝብን የመታደግ እርምጃ የሚወሰድበት አመት ይሆናል” አለ

 (ስምንት)ቀን ፳፻፮ /  ኢሳት ዜና :-ህዝባዊ ሀይሉ የተመሰረተበትን አንደኛ አመት በማስመልከት ባወጣው መግለጫ ” ያለፈው አንድ አመት የመሰባሰብ ድርጅት መሰረታዊ የሆኑ የፖለቲካና የወታደራዊ ስልጠና የተሰጠበት፣ የድርጅት ማጠናከሪያና የማጥራት ሂደት የተካሄደበት ” ነበር ብሎአል። መጪውን አመት የተለየ የሚያደርገው ህዝባዊ ሀይሉ በህዝብ ላይ በሚደርሰው ግፍና ውርደት ከሚሰማው ከፍተኛ ብስጭትና ቁጭት አልፎ ባለፈው አመት ሊደርስላቸው ያልቻለውን የአገራችንን ግፉአን ህዝቦች መታደግ የሚችልበትን እርምጃዎች መውሰድ የሚችልበት መሆኑ ነው” የሚለው ህዝባዊ ሀይሉ፣ በዚህ የህዝባዊ ሀይሉ የአንደኛ አመት ምስረታ ክብረ በአል ወቅት ለወገንም ለጠላትም በግልጽ እንዲያውቀው የምንፈልገው ይህን ሃቅ ነው ብሎአል።
ህዝባዊ ሀይሉ ” ለተራ የፕሮፓጋንዳ ፍጆታ ስንል በቂ ዝግጅት ያልተደረገበት የሃገሪቱን ውድ ልጆች በከንቱ የሚማግድ ጀብደኛ እንቅስቃሴ  አናደርግም። በውሸት ተስፋ  ህዝብን አንመግብም።  አይናችንን ከዋናው የኢትዮጵያና  የህዝቧ  ጠላት ከሆነው ከወያኔ ላይ አንስተን በሌሎች  ወያኔን እቃወማለሁ በሚሉ ሃይሎች ላይ አንተክልም። ከወያኔ ሌላ ወደ ጎን የምንዋጋው፣ የምንጨቃጨው አታካራ የምንገጥመው ምንም ሃይል አይኖርም። ወያኔን ለመምታት ህዝባዊ ሃይሉ የጨበጠው  ቡጢ ወገኖቻችን በፍቅር ለመጨበጥ የሚዘረጉ ጣቶች  እንዳሉት በጸረ ወያኔ ዴሞክራሲያዊ ትግሉ  ከልባቸው ለመተባበር ለሚፈልጉ ሃይሎች ሁሉ ግልጽ እናደርጋለን።” ሲል አትቷል።
በግንቦት7 ህዝባዊ ሀይል አመራሮች ላይ መንግስት የመግደል ሙከራ ማድረጉና መክሸፉ ይታወሳል።  በቅርቡ ደግሞ ከአመራሩ ጋር ለመደራደር ጥያቄ ማቅረቡና ንቅናቄው ውድቅ ማድረጉ ይታወቃል።

Tuesday, December 17, 2013

የግንቦት 7 ህዝባዊ ሃይል የተመሰረተበትን አንደኛ አመት አስመልክቶ የተሰጠ ድርጅታዊ መግለጫ


ቀን ታህሳስ 7 2006
ታህሳስ 7 2006 ዓም የግንቦት 7 ህዝባዊ ሃይል ከተመሰረተ አንድ አመት ሞላው። አንድ አመት በጭንቅና በአሳር ለተያዘች የዛሬይቱ ኢትዮጵያና ህዝቧ እጅግ ረጅም ግዜ እንደሆነ ህዝባዊ ሃይሉ በሚገባ ይገነዘባል። ባላፈው አንድ አመት ውስጥ የኢትዮጵያን ህዝብ የመከራ፣ የአሳርና የውርደት ህይወት ይበልጥ እየሰፋ፣ የሚፈጸምበት ግፍ ይበልጥ እየገዘፈ መሄዱን አይተነዋል። በሃገርና በህዝብ ላይ እየወረደ ያለውን ወያኔ ወለድ የስቃይና የፍዳ ናዳ በቅጡ ላጤነው ሃገሪቱና ህዝቧ የአዳዲስ የስቆቃና የመከራ አይነቶች መፈተኛ ቤተ ሙከራዎች እየተደረጉ ለመሆኑ ጥርጥር አይኖረውም። ለሚራበው፣ ለሚረገጠው፣ በግፍ ለታጎረው፣ በኑሮ ውድነት ለሚጠበሰው፣ ለተሰደደው ለተፈናቀለው ኢትዮጵያዊ እንድ አመት በሲኦል የቀናትና የወራት መቁጠሪያ እንደሚለካ ዘመን እጅግ የረዘመ የስቃይ ግዜ ነው።
የዋልድባ መነኩሳት ገዳማችን አትድፈሩ አታፍረሱ በማለታቸው እየተገረፉ ለዘመናት ፈጣሪያቸውን ከሚማጸኑበት ለሃገርና ለህዝብ ምልጃ ከቆሙበት ገዳም በዘር መመዘኛ እየተለዩ እንደቆ ሻሻ ተጠርገው የተባረሩበት፣ እምነታችን አትንኩ ያሉ የእስልምና እምነት ተከታዮችና መሪዎቻቸው በሃሰት ክስ ተመስርቶባቸው ወህኒ መውረዳቸው አንሶ ወንድሞቻችን ይፈቱ በማለት ሰላማዊ ጥያቄ ያቀረቡ ወገኖቻቸን በወያኔ ነፍሰ ገዳዮች በአረመኔያዊ ጭካኔ የተጨፈጨፉት በዚሁ አመት ነው። ወያኔ በህዝብ መሃከል በዘራው የዘር መርዝ የተነሳ በሽዎች የሚቆጠሩ አማሮች ከጉራ ፈርዳና ከቤንሻንጉል፣ ኦሮሞዎች ለዘመናት ከኖሩበት ምስራቅ ሃረርጌ አካባቢ እንዲፈናቀሉና በገዛ ሃገራቸው መድረሻ ቢሶች እንዲሆኑ የተደረገው በዚህ አንድ አመት ውስጥ ነው። ጋምቤላዎች ሙርሲዎች አፋሮችና ሌሎችም ብሄረሰቦችና ማህበረሰቦች የተጨፈጨፉበት፣ በልማት ስም ለመጡ የውጭ ወራሪዎችና ወያኔ ለፈጠራቸው ቱጃሮች ቦታ እንዲለቁ ተደርጎ ቀደምቶቻቸው ለዘመናት ከኖሩባቸው ቀየዎች እንዲነቀሉ ተደርገው እንደ አልባሌ ነገር የትም እንዲበተኑ የማድረጉ ሂደት ከመቼውም በላይ ተጠናክሮ የቀጠለው በዚሁ አመት ነው። በዚሁ አንድ አመት በወያኔ የሃገሪቱ ገዥዎች በህዝብ ላይ የተፈጸመው ጭካኔና ወንጀል ተዘርዝሮ የሚያልቅ አይደለም።
ይህ ወያኔ ሰራሽ ሃገር በቀል የውርደትና የስቃይ ህይወት አልበቃ ብሎ ወያኔ ከሳውዲ የጨለማ ዘመን ገዥዎች ጋር በመተባበር ወንድሞቻችን በሳውዲ አውራ ጎዳናዎች ላይ እንዲታረዱ እህቶቻችን በቡድን በተደራጁ የሳውዲ ጎረምሳዎች እንዲደፈሩ ሁኔታዎችን አመቻችቶ ለኢትዮጵያውያን ያለውን እጅግ የከረረ ጥላቻ በአደባባይ ያሳየበት አመት ነው። እንዲህ አይነቱ የጅምላ ግፍና ውርደት ከመከሰቱ በፊት ህዝባዊ ሃይሉ በአረብ ሃገር በባርነትና በስደት የሚገኙ እህትቶቻችንን ወንድሞችችን ስቃይ ስቃዩ አድርጎ በመውሰድ “ላንቺ ነው” በሚለው ድርጅታዊ መዝሙሩ “በባለጌ አረቦች መዳፍ ውድ ክብራቸው ለጎደፈው እህቶቻችን፣ በአረቦች የባርነት ቀንበር ጀርባቸው ለጎበጠው ወገኖቻችን እንደርስላችኋለን፣ የተሰባሰብነው ደማችን የሚፈሰው የመከራ ቀናችሁን ለማሳጠር ነው” የሚል ቃል ኪዳኑ ሰጥቶ ነበር። የድርጅታችንን ምስረታ አንደኛ አመት ስናከብር ልባችንን ደስታ ሳይሆን ሃዘን እንዲሞላ የሚያደርገው ይህ ቃል ኪዳናችን ለማክበር የጀመርነው ጉዞ ከድርጅት ምስረታና ከድርጅታዊ ዝግጅት አልፎ በኢትዮጵያ ህዝብ ጥላቻና ንቀት የተነፋውን የወያኔን እብሪት በማስተንፈስ የወሰዳቸው ተጨባጭ የአለኝታነት እርምጃዎች ባለመኖራቸው ነው።
ምንም እንኳን ግንቦት7 ህዝባዊ ሃይል እራሱን እንደ ድርጅት አቁሞ ኢትዮጵያውያንን አሰባስቦ መራራው ትግል የሚጠይቀውን የፖለቲካ የወታደራዊ ስልጠናና ትጥቅ አስታጥቆ በወያኔ ላይ ለመዝመት የጀመረውን ጉዞ የሚያስቆመው ምድራዊ ሃይል እንደሌለ ብናውቅም የህዝብ ስቃይ ለግዜው መቀጠሉ የህባዊ ሃይሉን አባላት ማሰቃየቱ አልቀረም። በወያኔ ግፈኛ አገዛዝ የተንገፈገፈው ወገናችን ህዝባዊ ሃይሉ የወያኔን አገዛዝ እድሜ የሚያሳጥሩ ፈጣን እርምጃዎችን እንዲወስድ በከፍተኛ ጉጉት እየተጠባበቀ እንደሆነ እናውቃለን። ህዝባዊ ሃይሉን ለመቀላቀል በመቶ ሽዎች የሚቆጠሩ የሃገሪቱ ዜጎች በተጠንቀቅ እንደቆሙ እናውቃለን። እነዚህ ዜጎች ከሁሉም የእምነት የቋንቋ የጾታ የእድሜ የኑሮና የማህበረሰብ ስብጥር የሚያካተቱ እንደሆኑ እናውቃለን። በሃገሪቱ ታሪክ ተሰምቶና ታይቶ በማይታወቅ ደረጃ የወታደር ልብሱን እየጣፈ እንዲለብስ፣ የወታደር ጫማውን መቀየሪያ አጥቶ ሸበጥ እንዲያደርግ የተገደደውን፣ የወያኔ ጀነራሎች በስልጣንና በዘረፋ ሲያብጡ በድህነት እንዲሟሽሽ የተፈረደበት የሃገሪቱ ሰራዊት በዘር በእምነት ሳይለያይ ከህዝባዊ ሃይሉ ጎን ለመቆም አሰፍስፎ የቆመ እንደሆነ እናውቃለን። ይህ ሃገራዊ እውነታ ለህዝብ የገባነውን ቃልኪዳን የለምንም ጥርጣሬ ማስከበር እንደምንችል በሙሉ ድፍረት እንድናውጅ የሚያስችለን ሃቅ ነው።
የወያኔ ጀንበር እየጠለቀች የኢትዮጵያ ህዝብ ጀንበር እየፈካች የመሄዱ ጉዳይ እንደማይታጠፈው የመንጋትና የመምሸት የተፈጥሮ ህግ ነቅነቅ የማይል እንደሆነ ግንቦት7 ጠንቅቆ ያውቃል። እውቀታችን ልዩ ጥበብ የሚጠይቅ ኣይደለም። ግፍ ፍትህን አሸንፎ፣ እውነት በሃሰት ተደፍቃ፣ ጥላቻ ፍቅርን፣ አድሎ እኩልነትን፣ ሃገራዊ ክህደት ሃገር መውደድን፣ ባንዳነት አርበኛናትን ለዘላላሙ ቀብረው የሄዱበት የሃገራችንና የሰው ልጆች ታሪክ የለምና የወያኔን አይቀሬ ሞት ለመተንበይ ልዩ ጥበብ አያሻንም። ይህን እኛ ብቻ ሳንሆን በዘረፋና በጥላቻ የደነዘዘ ህሊና ያዳበሩት የወያኔ ባለስልጣናትም ያውቁታል። ያለእኔ ጀግና የለም፣ ያለእኔ አልሞ ተኳሽ የለም በሚል እብሪት በመጻደቅ የሚታወቁት ወያኔዎች በመቶ ሽዎች በሚቆጠሩ ወታደሮች ተከበው፣ በታንክ በአይሮፕላን በሚሳይል ታጅበው ከሚኖሩበት ቤተመንግስትና ቪላዎች ውስጥ ብርክ እንዲይዛቸው ያደረገው ለመሆኑ፣ ሳር ቅጠሉ ግንቦት ሰባት እየመሰላቸው ሲበረግጉ እንደሚያመሹ፣ የግንቦት ሰባት አባላት እያሉ ከድርጅታችን ጋር አንዳችም ግንኙነት የሌላቸውን ዜጎች እያሰሩ ሲያሰቃዩ፣ ከምላሳቸው ላይ ግንቦት 7 የሚል ስም ተፈናጦባቸው እንደሚውሉ በራሳቸው ሚድያ ወያኔዎች ራሳቸው እያሳዩን እያስደመጡን ነው። ከዚህም አልፎ በዚህ አንድ አመት ውስጥ የህዝባዊ ሃይሉን መሪዎች በመግደል ድርጅቱን ለማኮላሸት ይቻላል በሚል ወያኔ የላካቸው ነፍሰ ገዳዮችና ድርጅቱን ከውስጥ ለመቦርቦር ያሰማራቸው ሰርጎገቦች ተራ በተራ ተልእኳቸው እየከሸፈ በህዝባዊ ሃይሉ እጅ እየወደቁ ወይም ተልእኳቸው እንደማይሳካ ሲረዱ እየፈረጠጡ ወደ ወያኔ ሲመለሱ አይተናል።
ያለፈው አንድ አመት ተመክሯችን ስለወያኔ ብቻ ሳይሆን ስለራሳችንም ጥንካሬና ድክመት ብዙ ነገሮች ያስተማረን ኣመት ነው። የቀደምቶቻችን የጀግንነት የአርበኛነት ቅርስ በመላ ህዋሳቸው የተሸከሙ ለኢትዮጵያ እና ለህዝቧ ሲሉ ደማቸው ለማፍሰስ ውድ ህይወታቸውን ለመሰዋት ወደኋላ የማይሉ ቆራጥ ብቻ ሳይሆኑ አርቀው የሚያዩ በርካታ ልጆች ሃጋሪቷ ያሏት መሆኑን ያረጋገጥንበት አመት ነው። በሌላ በኩል ደግሞ ድርጅታችን የኢትዮጵያን ህዝብ ብቸኛው የመንግስት ስልጣን ባላቤት የማድረጉን ታሪካዊ ራእዩን ለመሳካት የሚያደረገው ትግል ከወያኔ ጋር ብቻ ሳይሆን ከራሳችንም ጋር የሚደረግ እንደሆነ በሚገባ የተረዳነው በዚሁ የአንድ አመት የድርጅታችን እድሜ ነው። ከራሳችን ጋር የሚደረግ ትግል ወያኔ በማህበረሰባችን ውስጥ ከዘራቸውና የሃገሪቱን ዜጎች እንዲበክሉ ካደረጋቸው የዘረኛነት የአድሎ ከህዝብና ከሃገር ጥቅም በፊት የራስን ጥቅም ማስቀደም፣ የሱሰኛነትና የሙስናና ሌሎችም አደገኛ ባህሎች ጋር ነው።
ህዝባዊ ሃይሉ ደግሞ ደጋግሞ እንደገለጸው ትግላችን አንድ መንግስታዊ ስርአት ወድቆ ሌላው የመንግስት ስርአት በመጣ ቁጥር የህዝብ ተስፋ እየጨለመ “አዲስ ከመጣው ስርአት ያላፈው ያረጀ ስርአት በግፈኛነቱ በዘራፊነቱ ያነሰ ነበር” የሚል የግፈኛና የዘራፊ ስርአቶች ንጽጽር ላይ የቆመ አሳዛኝ የህዝብ ህይወት እንዲያበቃ ነው። ደርግን ያየ የአጼውን ስርአት እንከኖች ረስቶ ንጉሱ ይሻሉን ነበር ያለበት፣ ወያኔን ያየ የደርግን አስከፊ ዘመን ረስቶ መንጌ በስንት ጣሙ ያለበት አሳዛኝ ሁኔታ ከወያኔ መውደቅ በኋላ በሃገራችን እንዳይደገም ነው ትግላችን። የኢትዮጵያ ህዝብ የውድ ልጆቹን ህይወት ገብሮ ወያኔን በማስወገድ የሚያመጣው ስርአት ከወያኔ ብሶ ህዝብ ወያኔ ማረኝ የሚልበትን ቅስም ሰባሪና አዋራጅ የታሪክ ቅጥልጥሎሽ እንዳይቀጥል ማድረግ ህዝባዊ ሃይሉ የተመሰረተበት፣ አባላቱ መከራ ለመቀበልና መስዋእትነት ለመክፈል በረሃ የገቡበት ዋናውና ብቸናው ምክንያት ነው። ትግላችንን መራራ የሚያደርገው ከበሰበሰውና የአንድ ጀምበር የህዝብ ቁጣ ከታሪክ ቆሻሻ የመጠያ ስፍራ ከሚከምረው የወያኔ ስርአት ጋር ብቻ ሳይሆን በወያኔ ቦታ የሚተካውን ስርአት ከአድሎና ከዘረኛነት ከዘረፋና ሃገራዊ ክህደት የጸዳ፣ ዳግም ለኢትዮጵያውያን ውርደትና እንግልት ምክንያት እንዳይሆን ለማድረግ ከራሳችን ጋር ሳይቀር የማያቋርጥ ትግልን ማድረግ የግድ ስለሚል ነው። ህዝባዊ ሃይሉ የአመጽ ትግል የሚያደርግ፣ የመሳሪያው ብዛትና የሰራዊቱ ቁጥር እያደገ የሚሄድ ሃይል መሆኑን ስለምንረዳ ይህን ሃይል ገና ከጅምሩ ከብዙ እንከኖች እያጸዱ ማደራጀት ካልተቻለ በሃገርና በህዝብ ላይ የሚመጣውን አደጋ የህዝባዊ ሃይሉ አባላት ጠንቅቀው የተረዱት ሃቅ ነው። ይህ ግንዛቤ የሰራዊቱን አባላት በጥንቃቄ መመልመልን፣ ማሰልጠንንና መገንባትን የግድ የሚል ነው።
ይህ ከራሳችን ጋር የሚደረግ ትግል እጅግ መራራ ነው። ታሪካዊ ስህተቶችን ላለመድገም የሚደረግ ትግል ነው። ይህ ትግል የአካልና የመንፈስ ጽናትን፣ ሃቀኛነትን፣ ታማኝነትን፣ ጀግንነትን የሚጠይቅ ትግል ነው። የወያኔ ስርአት ከሃገር ግድያው በተጨማሪ ትውልድን ለመግደል ሆን ብሎ ያስፋፋቸው እኩይና ጎጂ ባህሎችና ልምዶች ምን ያህል ማህበረሰባችንን እንደጎዱት ህዝባዊ ሃይሉ ባላፈው አንድ አመት እድሜው በሚገባ የተረዳው ጉዳይ ሆኗል። ህዝባዊ ሃይሉ የሚመኘውን የኢትዮጵያ ትንሳኤና ተሃድሶ እውን ለማድረግ እነኝህ ወያኔ ሆን ብሎ ያስፋፋቸውን የባህልና የሞራል ብክለት ማጽዳት የግድ እንደሆነ የተረዳ አካል ሆኗል።
ትግላችን መደፍረስን መጥራትን፣ መንተክተክን መስከንን የትግሉ ሂደት አካል አድርጎ የሚጓዝ ነው። ትግሉ የሚልመጠመጠውን እንደቀስት ቀጥ ብሎ ከሚራመደው፣ በካፊያው የሚንቀጠ ቀጠውን ለዶፉ ደንታ ከሌለው፣ ዝናር በቅፌን ከምሩ ተኳሽ የሚለይ መራራ ትግል ነው። ያለፈው አንድ አመት ይህን አስተምሮናል። ህዝባዊ ሃይሉ ትግሉ ቀላል ነው የሚል ከእውነታ ጋር ያልተያያዘ ቃል ለህዝብም ሆነ ህዝባዊ ሃይሉን ሊቀላቀሉት ለተዘጋጁት ወገኖቹ አይናገርም። ህዝባዊ ሃይሉን ለመቀላቀል ለተሰለፉ በሽዎች ለሚቆጠሩ ወገኖቻችን ትግሉ የሚጠየቅውን የሞራል የስብእና ጥብቅነት፣ከፍተኛ የሃገርና የወገን ፍቅር፣ ጥልቅ የሆነ የመስዋእትነት ፈቃደኛነት የሚጠይቅ መሆኑን ከማስረዳት አንቦዝንም። ህዝባዊ ሃይሉ ለህዝብ ቃል እንደገባው ከወያኔ ጋር የምናደርገው ትግል በጥበብ በእውቀት በጥናት በጥንቃቄ የምናደርገደው ነው። ነጻነት ያለመስዋእትነት እንደማይሳካ ብናውቅም ለተራ የፕሮፓጋንዳ ፍጆታ ስንል በቂ ዝግጅት ያልተደረገበት የሃገሪቱን ውድ ልጆች በከንቱ የሚማግድ ጀብደኛ እንቅስቃሴ አናደርግም። የውሸት ተስፋ ህዝብን አንመግብም። አይናችንን ከዋናው የኢትዮጵያና የህዝቧ ጠላት ከሆነው ከወያኔ ላይ አንስተን በሌሎች ወያኔን እቃወማለሁ በሚሉ ሃይሎች ላይ አንተክልም። ከወያኔ ሌላ ወደ ጎን የምንዋጋው፣ የምንጨቃጨው አታካራ የምንገጥመው ምንም ሃይል አይኖርም። ወያኔን ለመምታት ህዝባዊ ሃይሉ የጨበጠው ቡጢ ወገኖቻችን በፍቅር ለመጨበጥ የሚዘረጉ ጣቶች እንዳሉት በጸረ ወያኔ ዴሞክራሲያዊ ትግሉ ከልባቸው ለመተባበር ለሚፈልጉ ሃይሎች ሁሉ ግልጽ እናደርጋለን።
ያለፈው አንድ አመት የመሰባሰብ የድርጅት ምስረታ መሰረታዊ የሆኑ የፖለቲካና የወታደራዊ ስልጠና የተሰጠበት፣ የድርጅት ማጠናከሪያና የማጥራት ሂደት የተካሄደበት ነው። በዚህ ረገድ የተሰራው ስራ አጥጋቢ ውጤት አስገኝቷል። ስልጠናው፣ ድርጅት ማጠናከሩና ማጥራቱ ወደፊትም የሚቀጥል ነው። መጪውን አመት የተለየ የሚያደርገው ህዝባዊ ሃይሉ በህዝብ ላይ በሚደርሰው ግፍና ውርደት ከሚሰማው ከፍተኛ ብስጭትና ቁጭት አልፎ ባላፈው አመት ሊደርስላቸው ያልቻለውን የሃገራችንን ግፉአን ህዝቦች መታደግ የሚችልበትን እርምጃዎች መውሰድ የሚችልበት አመት መሆኑ ነው። በዚህ የህዝባዊ ሃይላችን የአንደኛ አመት ምስረታ ክብረ በአል ወቅት ወገንም ጠላትም በግልጽ እንዲያውቀው የምንፈልገው ይህን ሃቅ ብቻ ነው።
ውድመት ለዋናውና ለብቸኛው የኢትዮጵያ ህዝብና የኢትዮጵያችን ጠላት ለሆነው የወያኔ ገዥ ጉጅሌ!!!!
ድል በወያኔ ግፈኛ ስርአት አበሳውን ለሚያየው የመላው የኢትዮጵያ ህዝብ!!!!!!
የግንቦት 7 ህዝባዊ ሃይል የተመሰረተበትን አንደኛ አመት አስመልክቶ የተሰጠ ድርጅታዊ መግለጫ, Audio  (mp3)

ምንጭ: www.ginbot7pf.org


Monday, December 16, 2013

ሰማያዊ ፓርቲ በዲሲ ከተማ ያደረገው ሰብሰባ በከፊል

የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢንጅነር ይልቃል በአውሮፓ እና በአሜሪካ ላይ ፓርቲያቸውን በማስተዋወቅ ይገኛሉ :: ይህን አሰማልክቶ በዛሬው ቀን መስከረም 15 በዲሲ ከተማ ሰብሰባው በደማቅ ሁኔታ ተካሂዶ ተጠናቋል::
Blue party in DC
Blue party in Dc
Blue party in DC
Blue party in dc
Blue party in Dc

ኢትዮጵያ ወደ ሱዳን የተከለለውን መሬት ህጋዊ ማድረጓ ተሰማ



የሱዳን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አሊ ካርቲ “ከኢትዮጵያ ጋር ያለብንን የድንበር ልዩነት ለመፍታት ተስናምተናል” አሉ፡፡ ማክሰኞ ታህሳስ 1 ቀን 2006 ዓ.ም ወደ ካርቱም የተጓዙት ጠ/ሚኒስትር ኃ/ማሪያም ደሳለኝ ከአልበሽር ጋር እንደተወያዩ ታውቋል፡፡ የሱዳኑ ሚኒስትር እንዳረጋገጡት ሁለቱ ሀገራት የሚወዛገቡበት የፋሻጋ አከባቢ ከንግድህ ያለመግባባት ምንጭ አይሆንም ብለዋል፡፡ የሱዳን ባለስልጣናትን እያጓጓ ያለው የሁለቱ ሀገራት መሪውች ስምምነት በኢትዮጵያውያን በኩል ከፍተኛ ጥርጣሬ አጭሯል፡፡
ከድንበር በተጨማሪ በዚህ የፊርማ ስነ-ስርዓት ላይ የተካተቱት የደህንነት፣ የኢኮኖሚ፣ የግብርና፣ ትምህርትና ባህል ጉዳዮች ኢትዮጵያ ያጣችውን ድንበር ለመሸፈን የተደረገ ማጀቢያ እንደሆነ አስተያየቶች እየተሰነዘሩ ናቸው፡፡ በጉዳዩ ላይ ያነጋገርናቸው አንድ አንጋፋ ፖለቲከኛ ኢህአዴግ የሀገርን የድንበር ሉዓላዊነትን ያስከብራል የሚል እምነት እንደሌላቸው ገልፀዋል፡፡
በሰሜን ጎንደር ዞን ታች አርማጮህ ወረጃ ነዋሪ የሆኑ ሌላ አስተያየት ሰጪ በበኩላቸው “ከዚህ በፊት ጥጃ ያሰርንባቸው መሬቶች ዛሬ ወደ ሱዳን ተከልለዋል፤ የራሳችንን መሬት ተከራይተን ነው የምናርሰው፤ ስለዚህ የፊርማ ስነ ስርዓቱ ይህንኑ ለሱዳን የተሰጠ መሬት ህጋዊ ለማድረግ ነው” ብለዋል፡፡

Thursday, December 5, 2013

መድረክ የጠራው ሰልፍ ተከለከለ


የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ አንድነት መድረክ (መድረክ) ህዳር 29 ቀን 2006 ዓ.ም ለማድረግ ያሳወቀው ሰልፍ ተከለከለ፡፡ መድረክ ሰልፉን ለመጥራት በሀገራችን መሰረታዊና ወቅታዊ የሆኑ ችግሮችን እንዲሁም በሰውዲና በአለም ዙሪያ በኢትዮጵያውያን ላይ እየደረሰ ያለው ሰቆቃ መሰረቱ የስደት መንስኤው ላይ በመሆኑ መንግስትን በሰላማዊ ሰልፍ ለመጠየቅ እንደነበር ለማወቅ ችለናል፡፡

ሰልፉን ለማድረግ የታቀደው ስድስት ኪሎ ዩኒቨርሲቲ አምስተኛ በር ፊት ለፊት ከሚገኘው የመድረክ ቢሮ በመነሳት በአምስት ኪሎና ስድስት ኪሎ አድርጎ ወደ ጠቅላይ ሚኒስትር ፅ/ቤት ድረስ ለመጓዝ ነበር፡፡ ነገር ግን የአድስ አበባ ከተማ አስተዳደር የከንትባ ፅ/ቤት “ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ እውቅና የጠየቃችሁበት ስፍራ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የስብሰባና የሰላማዊ ሰልፍ አሰራር ስነ-ስርዓት አንቀፅ አምስት ሀ እና መ የሰላማዊ ሰልፍ የማይካሄድባቸው ቦታዎች ተብለው የተጠቀሱ በመሆናቸው የተጠየቀው የሰላማዊ ሰልፍ እውቅና መስጠት የማንችል መሆናችንን እንገልፃለን” ሲል መልስ ሰጥቷል፡፡

በጉዳዩ ላይ አስተያት እንዲሰጡ የጠየቅናቸው የመድረክ ስራ አስፈፃሚና የአንድነት ፓርቲ ዋና ፀሀፊ አቶ አስራት ጣሴ “መልሱ የመድብለ ፓርቲ ቅልበሳ ከመሆን አይዘልም” ይላሉ፡፡ አስተዳደሩ ጠቅሶ እውቅና ለመንፈግ የተጠቀመበት ደንብ ማንም የሚያውቀው መሆኑን የተናገሩት አቶ አስራት በማያውቁት ህግ እንደማይደኙ ገልፀውልናል፡፡ በተጨማሪ በዚህ ጉዳይ ላይ የወጣው አዋጅ መወቅ ቢችሉ እንኳ በተባለው ደንብ እንደማሻር አክለዋል፡፡

በ1983 ዓ.ም የወጣው የሰላማዊ ሰልፍና ህዝባዊ ስብሰባ አዋጅ (አዋጅ ቁጥር 3 1983) የተከለከሉ ብሎ የሚጠቅሳቸው ቦታዎች እንደሌሉና ከኤምባሲዎች፣ ት/ቤቶች፣ ሆስፒታሎች፣ የሀይማኖት አምልኮ ስፍራዎች፣ በገበያ ቀን (ከገበያ ስፍራ) መቶ ሜትር መራቅ እንዳለበት ማዘዙን አቶ አስራት ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም ከጦር ካምፕና የደህንነት ተቋማት 500 ሜትር መራቅ እንዳለበት አዋጁ ማስገደዱን ያስረዱት አቶ አስራት ከዚህ ቀደም አንድነት መስከረም 19 ቀን 2006 ዓ.ም በጠራው ሰልፍ ይህንን አዋጅ በመሻር በጦር ካምፕና በደህንነት መስሪያቤቶብ በተከበበው ጀንሜዳ እንድንወጣ ነግረውናል ብለዋል በተሰጠው መልስ ላይ አቋም ለመያዝ የመድረክ አመራር እንደሚሰበሰብ ከአቶ አስራት ጣሴ ለማወቅ ችለናል፡፡

መድረክ ህዳር 5 ቀን 2006 ዓ.ም መድረክ ለጠራው ሰልፍ አስተዳደሩ ከተደራራብ የስብሰባ ጫና የተነሳ የፖሊስ ሀይል ስለሌለኝ ጥበቃ ለማድርግ አልችልም በሚል እውቅና መንፈጉ ይታወቃል፡


ወንድማችን ሙሐመድ ኢብራሒም ከ29ቀናቶች የማእከላዊ ስር ቦሀላ ዛሬ ሂወቱ ማለፉ ተሠማ !!!!!!::


Very sad news

Ethio Bilal Tube
Bilal Communication
Ina Lilahi We Ine Ilahi Raje’un
   ሰበር ከአዲስ አበባ    ቦሌ ሚካኤል ቀበሌ 01
ወንድማችን ሙሐመድ ኢብራሒም ከ29ቀናቶች የማእከላዊ ስር ቦሀላ ዛሬ ሂወቱ ማለፉ ተሠማ
በንግድ ስራ ይተዳደር የነበረዉ ወንድማችን ሙሐመድ ኢብራሂም መንግስት አሸባሪ ነክ
ብሎ በኢትዮጲያ ጎንታናሞ ማእከላዊ ለእስር ከዳረገዉ በኃላ
ከፍተኛ ድብደባና ስቃይ ካደረሱበት
ቦኃላ ዛ ለህልፈተ ህይወት ዳርገዉታል
በ29ቀናት የእስር ቆይታዉ በቤተሠቦች እንዳይዘየር ተደርጎዋል ወንድማችን ሙሐመድ የሰባት ልጆች አባት የነበረና አምስት ወቅት ሰላት ከመስጂድ የማይታጣ ነበር
በርካታ ምዕመናን በተገኙበት በጃፈር መስጂድ ሶላተል ጀናዛ ከተሰገደበት ቦኃላ በላፍቶ እስላም መቃብር የቀብር ስነስራቱ ተፈጽመዋል
ወንድማችንን አሏህ ከሹሐዳዎች ያድርገዉ ለቤተሰቦቹ መጽናናትን ይስጣቸዉ ::

Tuesday, December 3, 2013

የወያኔ አገዛዝ በመልዕክተኞቹ በኩል ላቀረበው የ“እንደራደር” ጥያቄ ከግንቦት 7 የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ የተሰጠ ምላሽ


ወያኔ ኢትዮጵያ ዉስጥ የገነባዉ ሥርዓት በከፍተኛ ችግሮች የተወጠረ ነው። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ የመሪው ሞት በወያኔ መሀል ያስከተለው ቀውስ፤ የሕዝብ ሁለገብ ትግል ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጎለበት መሄድ የፈጠረበት ስጋት እና ምርጫ በደረሰ ቁጥር የሚደርስበት ጭንቀት መጨመር ተደማምረው ውጥረቱን ወደ ከፍተኛ ደረጃ እያደረሱት መሆኑን የሚያሳዩ በቂ ምልክቶች አሉ። የእስካሁኑ ተሞክሮዓችን እንደሚያሳየው ወያኔ ውጥረት ሲበዛበትና መዉጪያና መግቢያዉ ሲጠፋዉ ፣ ተቃዋሚ ድርጅቶችን “እንወያይ፣ እንደራደር” በማለት ለውጥረት ማስተንፈሻ ጊዜ የሚገዛ መሆኑን ነው። ሰሞኑን በወያኔ አገዛዝ መልዕክተኞች በኩል የደረሰንን “የእንደራደር” ጥያቄ ንቅናቄያችን በዋናነት ያየው ወያኔ እንደለመደው ድርድርን ለውጥረት ማስተንፈሻነት ለመጠቀም እየሞከረ መሆኑን ነው።
የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚመኘው ዲሞክራሲያዊ ለውጥ በሰላማዊ መንገድ በሚደረግ ትግልና በጠረጴዛ ዙሪያ በሚደረጉ ዉይይቶች ቢመጣ የግንቦት 7 ምርጫ መሆኑን ንቅናቄያችን በተደጋጋሚ ግልጽ አድርጓል። ግንቦት 7ን ሁለገብ ትግል ውስጥ እንዲገባ ያስገደደው የወያኔ እምቢተኝነትና እብሪት ብቻ ነው።
የግንቦት 7 ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ የሰሞኑ የወያኔ የእንደራደር መልዕክት እንደደረሰው በጉዳዩ ዙሪያ በሰፊው ከተወያየ በኋላ ይህ ጉዳይ የኢትዮጵያን ሕዝብ ባጠቃላይ እንጂ ግንቦት 7ን ብቻ የሚመለከት ጉዳይ እንዳልሆነ ከድምዳሜ ላይ ደርሷል። ይህ ጉዳይ የኢትዮጵያ ሕዝብ ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ ከሚያደርገው ትግልና እየከፈለ ካለው መስዕዋትነት ጋር በቀጥታ ግንኙነት አለው። በመሆኑም፤ ለቀረበልን ጥያቄ ግልጽ መልስና፤ ድርድር ስለሚባለው ጉዳይም ያለንን አቋም ጉዳዩ በቀጥታ ለሚመለከተው የኢትዮጵያ ሕዝብና የተለያዩ የፖለቲካ ድርጅቶች ሁሉ ለማቅረብ የሚያስችል ተጨማሪ አጋጣሚ አድርገን ወስደነዋል። በዚህም መሠረት ለቀረበልን ጥያቄ የሰጠነዉን መልስና አቋማችንን በድርጅታችን ድረ ገጽ ላይና በሌሎች መገናኛ ብዙሀን በኩል በይፋ ለመግለጽ ወስነናል።
በድርድር ስለሚመጣ ለውጥ ያለን የመርህ አመለካከት:
ከዚህ በፊት በተደጋጋሚ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ግልጽ እንዳደረግነው ድርጅታችን ከምሥረታው ጀምሮ የትግል ስልቱን ሲወስን እምነቱ አድርጎ የተነሳው ዴሞክራሲያዊ ለውጥ በሀገራችን በሰላማዊ መንገድና በድርድር ቢመጣ በእጅጉ የሚፈልገውና የሚመኘው መሆኑን ነው:: ድርጅታችንን ወደ ሁለንተናዊ ትግል የገፋው በመግቢያው ላይ እንደገለጽነው የወያኔ እብሪት ብቻ ነው:: የቀረበልን ምርጫ በባርነትና በውርደት መኖር ወይም ለነፃነት እየታገልን መሞት ቢሆን ኖሮ ንቅናቄያችን የሚመረጠው ምን ግዜም ለነፃነትና ለአገር አንድነት ታግሎ በክብር መሞት መሆኑን በተደጋጋሚ ለሕዝብ ግልጽ አድርገናል። ይህ የማይናወጥ አቋማችን ደግሞ ለይምሰል የተቀመጠ አቋም ሳይሆን ከልባችን የምናምንበትና ኢትዮጵያን ጨምሮ በዓለም ዙሪያ የሚገኙ አባላቶቻችንን ያሰባሰብንበት አቋም ነው። ዛሬ በትግሉ ግንባር የምንንቀሳቀሰውና ወደ ግባችን የሚወስደንን ተጨባጭ እርምጃዎች እየወሰድን ያለነውም በዚሁ አቋማችን ዙሪያ ነዉ።
ይህ አቋማችንና እምነታችን በአንድ ላይ ጎን ለጎን የሚሄዱ ሁለት መርሆችን አጣምሮ የያዘ ነዉ። አንደኛው፣ ሂደትን በሚመለከት ሁሌም ለድርድር ክፍት መሆኑን የሚያመለክት ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ፣ ይህ የድርድር ሂደት እንዲያው ለለበጣ የሚደረግ ሳይሆን ወደሚፈለገው ነጻነት በአነስተኛ መስዕዋትነት ሊያደርስ ይችል ከሆነ በሩን ላለመዝጋት እንጂ፣ በምንም አይነት ዋና ውጤቱን፤ ማለትም ኢትዮጵያን እውነተኛ ዴሞክራሲያዊ ሀገር ማድረግን፤ የሚቀይር ወይንም ከዚያ ያነሰ ውጤትን ለመቀበል መፍቀድን ፈጽሞ የማያመለክት መሆኑን ነው::
በእኛ በኩል ድርድሩን አስፈላጊና ጠቃሚ የሚያደርጉት መነሻ የፖለቲካ እሳቤዎችም ከእነኝሁ ሁለት መንታ ገጽታዎች የሚመነጩ ናቸው:: በድርድር ለሚገኝ ፍትሀዊና እውነተኛ ውጤት ክፍት መሆናችንን ሁሌም እናሳያለን፤ ነገር ግን ይህን የምናደርገው የሕዝብ የሥልጣን ባለቤትነት የተረጋገጠባትን ኢትዮጵያን እውን ማድረግ የሚጠይቀውን ማንኛውንም መስዋዕትነት መከፈል አለበት የሚለውን መሠረታዊ የአካሄድ መርህ በመመርኮዝ እንጂ መርሀችንን ለድርድር ለማቅረብ እንዳልሆነ በግልጽ መታወቅ ይኖርበታል::
ስለዚህም:
ሀ)    የድርድሩ ውጤት የኢትዮጵያን ሕዝብ የሥልጣን ባለቤትነት ያረጋገጠ የዴሞክራሲያዊ ሥርዓትን በአስቸኳይ እውን ማድረግ መሆን ይኖርበታል:: ይህ ዋናው ግብ ሆኖ ከዚህ በመለስ የሚኖሩ በሂደት የሚገኙ አነስተኛ ግቦች ሊኖሩ ይችላሉ (ለምሳሌ የፖለቲካ እስረኞች ማስፈታት…ወዘተ):: ሆኖም በምንም አይነት ለእነኝህ መለስተኛ ግቦች ተብሎ ዋናውን ግብ የሚያሳጣ ወይንም ጊዜውን ያላግባብ የሚያስረዝም ድርድር፣ ድርድር ነው ብሎ ድርጅታችን አይቀበልም። ስለዚህም ዋናው የድርጅታችን ዓላማና ግብ የሆነው የኢትዮጵያ ሕዝብ የሥልጣን ባለቤትነት ፣ በፍጹም ለድርድር የሚቀርብ ጉዳይ አይደለም:: በሥልጣን ላይ ባለው ኃይል በኩል ወደዚህ ግብ ለመድረስ ቁርጠኝነቱ በሌለበት ሁኔታ በሚደረግ ማንኛውም አይነት ድርድር ውስጥ ግንቦት 7 አይሳተፍም::
ለ)  በግንቦት 7 እምነት ማንኛውም ድርድር ወያኔ ከግንቦት 7 ጋር በተናጠል የሚያደረገው ሳይሆን ጉዳዩ የሚመለከታቸውን ሁሉንም የፖለቲካ ኃይሎች ያካተተ መሆን ይኖርበታል:: ድርጅቶችን በተናጠል እየለያዩ “እንደራደር” ማለት በራሱ ጊዜያዊ የፖለቲካ ጥቅም ስሌትን የያዘ እሳቤ እንጂ፣ በዘላቂነት አገሪቱን እውነተኛ ዴሞክራሲያዊ አገር ለማድረግ መፈለግን አያመለክትም:: ለአንድ ድርጅት ለብቻው የሚመጣ ወይም የሚጠቅም ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት የለም:: ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት የመፍጠር ፍላጎት ያለው ድርድር በአገሪቱ ያሉትን የተለያዩ የፖለቲካም ሆነ የሲቪክ ኃይሎችን ያካተተና ያመኑበት መሆን ይኖርበታል:: የሚደረገው ድርድርም ማን በስልጣን ላይ ይውጣ ወይንም የፖለቲካ ስልጣንን ባሉት ኃይሎች መሀከል እንዴት እናከፋፍለው የሚል የስልጣን ቅርምት ድርድር ሳይሆን፤ ሕጋዊና የሕዝቡን የሥልጣን ሉዓላዊነት ባረጋገጠ ሁኔታ የፖለቲካ ስልጣን እንዴት እንደሚያዝ ፍትሀዊ የሆነ ሂደትን ለማስጀመር የሚደረግ ድርድር መሆን አለበት::
ሐ) ቀደም ብለን እንደጠቀስነው ይህ ጉዳይ የሚመለከተው አንድን ድርጅት ወይንም የፖለቲካ ድርጅቶችን ብቻ ሳይሆን መላውን የኢትዮጵያን ሕዝብ ነው:: ይህ እስከሆነ ድረስ እንዲህ አይነት ድርድር ከሕዝቡ በተደበቀ ሁኔታ በሚስጥር የሚካሄድበት ምንም ምክንያት የለም::
2)   ከዚህ በፊት ከወያኔ ጋር ከተደረጉ ድርድሮች ያገኘናቸው ተመክሮዎችና ከዚህ በመነሳት ወደፊት በሚደረጉ ምንም አይነት ድርድሮች እንዳይደገሙ ለመጠበቂያ የሚሆኑ ከአሁኑ መወሰድ ያለባቸው እርምጃዎች
ከማንኛውም ወገን ጋር የሚደረግ ድርድር የተደራዳሪዎቹ ምንነት፤ ውስጣዊ ባህርያቸውን፤ ከተለምዶ ተግባራቸው ያላቸውን ተአማኒነትና ወደዚህኛው ድርድር ያመጣቸውን ምክንያቶች በበቂ ከመገንዘብ ጋር ተያይዞ የሚታይ ጉዳይ ነው:: ቃሉን አክባሪና ተዓማኒ ከሆነ ሰው ጋር የሚደረግ ድርድርና ያለፈው ታሪኩ ምንም አይነት የተዓማኒነት ባህርይ ከማያሳይ ቡድን ጋር የሚደረግ ድርድርም ሆነ ለድርድሩ የሚደረግ ዝግጅት ለየቅል ናቸው:: ይህ ማለት ግን ተዓማኒነት ካለው ኃይል ጋር ብቻ ነው ድርድር የሚካሄደው ማለት አይደለም:: በፍጹም ተዓማኒ ካልሆነ ኃይል ጋር የሚደረግ ማንኛውም ድርድር ግን ድርድሩ በእርግጥም ተግባራዊ ሊሆን የሚችል መሆኑን የሚያሳዩ ጠንካራ መጠበቂያዎች (System of Verification) እንዲሁም ግልጽ የመተግበሪያ ሥርዓቶች (Implementation Mechanism) ሲደረጉለት ብቻ ነው ከምር ሊወሰድ የሚችለው:: ከዚህም ባሻገር ግን መጀመሪያውኑ ወደ ድርድር የሚመጣው ለጊዜያዊ የፖለቲካ ጥቅም ሳይሆን በእዉነተኛ መንፈስ ከድርድር የሚመጣውን ውጤት በመፈለግ መሆኑን የሚያሳዩ “የመተማመኛ” ምልክቶች ሲያሳይ ነው በእርግጥም ወደ ድርድር የመጣው ከልቡ ድርድሩንና ከድርድሩ የሚመጣዉን ዉጤት ፈልጎ መሆኑን ለማመን የሚያስችለው::
ወያኔ ከተቀናቃኝ ወገኖች ጋር “ድርድር” ሲያደርግ የመጀመሪያ ጊዜዉ አይደለም:: እኛ እስከምናውቀው ድረስ ምናልባት በኃይል ይበልጡኛል ብሎ ከሚያምናቸው ወገኖች ጋር ካልሆነ በስተቀር፣ በረሃ ከነበረበት ጊዜ ጀምሮ በማንኛውም ጊዜ ለቃሉ ታማኝ፤ ለመርሁ እውነተኛ፤ ለደረሰበት ስምምነት ተገዢ ሆኖ አያውቅም:: ይልቁንም ሶስተኛ አደራዳሪ ወገኖችን በሚያሸማቅቅና በሚያሳፍር መልኩ ውሸትን እንደ አዋቂነት፤ ማጭበርበርን እንደ ብልጠት፤ የተስማማበትን በገሀድ ማፍረስን እንደ የአመራር ብልሀት አድርጎ የሚያይ፤ ምንም እፍረትና ጨዋነት የሚባል ነገር ያልፈጠረበት እኩይ ኃይል ነው:: ከራሱ የድርጅት ጥቅምና በስልጣን ከሚገኝ የዝርፊያ ሀብት ማካበት ባሻገር፤ ለአገር ዘላቂ ጥቅም ብሎ የራሱን ጥቅም አሳልፎ የሚወስደው ምንም እርምጃ እንደሌለ በተግባር በተደጋጋሚ ያረጋገጠልን ኃይል ነው:: በግንቦት 7 ውስጥ ያለን ወገኖች ይህንን የወያኔ ባህርይ በንድፈ ሀሳብ ደረጃ ሌሎች ጽፈውት ያነበብነው ሳይሆን፣ እራሳችን በተግባር በተሳትፈንበት ሂደት ያገኘነው ጥልቅ ግንዛቤ ነው:: ይህንን ደግሞ በአንድ አጋጣሚ ብቻ ሳይሆን ከድርጅቱ ታሪክ ጋር የተጣበቀ፤ በአመራር አባላቱ ላይ እንደ ግል ባህርይ የሰረጸ መሆኑን እስክንገነዘብ ድረስ በተደጋጋሚ የተመለከትነው ነው:: ስለዚህም ከዚህ ኃይል በኩል የሚመጣን የ “እንደራደር” ጥያቄ ከዚህ በፊት እንዳደረገው ለገባበት የፖለቲካ ውጥረት ማስተንፈሻ፣ ለውሸት ፕሮፓጋንዳው መጠቀሚያ፤ ለጊዜያዊ የፖለቲካ ትርፍ መሰብሰቢያ፤ የዴሞክራሲ ታጋዮችን ትጥቅ ማስፈቺያና ወኔ መስለቢያ አድርጎ እንዲጠቀምበት በፍጹም አንፈቅድለትም:: ስለዚህም ከላይ በመርህ ደረጃ ከጠቀስናቸው ሶስት ጉዳዮች በተጨማሪ ምንም ዓይነት ድርድር ከመደረጉ በፊት ወያኔ ጉዳዩን ከምር የወሰደው መሆኑን የሚያሳዩ “የመተማመኛ” እርምጃዎች መውሰድ አለበት ብለን እናምናለን::
እነኝህም፣
ሀ)  ሁሉንም የፖለቲካ እስረኞች፤ ጋዜጠኞች፤ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች ያለምንም ቅድመ ሁኔታ መፍታት:: ይህ ደግሞ በግልጽ     የሚታወቁ እስረኞችን ብቻ ሳይሆን በድብቅ የተቋቋሙ ማጎሪያና ማሰቃያ ቤቶች ያሉትን ሁሉ ማጠቃለል አለበት።
ለ)  በሕዝብ በተለይ በተቃዎሚ ኃይሎች ላይ ወያኔ በየቀኑ እያካሄደ ያለውን ወከባና እንግልት ባስቸኳይ ማቆም፣ ሰብዓዊና የዜግነት መብታቸውን ማክበር አለበት።
ሐ)   በፖለቲካ ምክንያት ከዚህ በፊት የተወሰዱ ሁሉም ዓይነት ፍርድ ተብዮ ውሳኔዎች እንዲሻሩ ማድረግ፤ በሂደት ላይ ያሉ ከፖለቲካ ጋር የተያያዙ ምንም አይነት ክሶችን ማቋረጥ አለበት።
መ)   ሕዝብን በፍርሃትና በስጋት ለማቆየት ሆነ ተብለው የወጡ አፋኝ ህጎችን በአስቸኳይ ማንሳት አለበት።
ሠ)   ማንኛውም ድርድር ገለልተኛ የሆኑ ሶስተኛ ወገኖች ባሉበት፤ የድርድሩ ሂደት በምስልና በድምጽ ተቀርጾ በገለልተኛ ወገኖች እጅ ብቻ የሚቀመጥ፣ የድርድሩ ቦታም የተደራዳሪ ወገኖች በጋራ በሚስማሙበት ቦታ መሆኑን መቀበልና ይህንንም በግልጽ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ማሳወቅ አለበት።
እነኝህ ከላይ ያስቀመጥናቸው በወያኔ በኩል የሚወሰዱ “የመተማመኛ” እርምጃዎች ለተቃዋሚዎች ተብሎ የሚወሰዱ እርምጃዎች አይደሉም:: ወያኔ እነዚህን እርምጃዎች ለመውሰድ ቁርጠኝነት ሳይኖረው ለእውነተኛ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት መመስረት የሚደረግ ድርድር ላይ ከምር ይሳተፋል ብለን ማመን በፍጹም ስለማንችል ነው ::
እስከዚያው ድረስ ግን ግንቦት 7ም ሆነ ሌሎች ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት መመስረት በቁርጠኝነት የምንታገል ኃይሎች፣ ወያኔ እነኝህን የመተማመኛ እርምጃዎች እስኪወስድና ቀደም ብለው በተቀመጡት መርሆች መሠረት በሚደረግ ድርድር በተግባር ሊመነዘር የሚችል ስምምነት፣ አልፎም ለምንም አይነት ማጭበርበርና መንሸራተት እድል የማይሰጥ ጠንካራ መጠበቂያዎች መኖራቸው እስኪረጋገጥ ድረስ፣ የጀመርነውን ትግል ይበልጥ አጠናክረን የምንገፋበት እንጂ በምንም አይነት ለአንድ አፍታም ቢሆን በድርድር ስም የማንዘናጋ መሆኑን አበክረን እናስታውቃለን::
የግንቦት 7: የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ፣
ኅዳር 23፣ 2006 ዓ:ም